የኢትዮጵያና የቀጠር ግንኙነት
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 27 2005
ኢትዮጵያና ቀጠር ከአራት ዓመት በፊት አቋርጠዉት የነበረዉን ዲፕሎማሲያዊና ምጣኔ ሐብታዊ ግንኙነት ለመቀጠል ተስማሙ።የሁለቱ ሐገራት ጠቅላይ ሚንስትሮች ትናንት አዲስ አበባ ዉስጥ ባደረጉት ስምምነት መሠረት ሁለቱ መንግሥታት ያለፈ ልዩነታቸዉን አስወግደዉ በተለያዩ መስኮች በጋራ የሚሠሩበትን ሥልት ቀይሰዋል።የሁለቱ ሐገራት የተለያዩ ሚንስትሮምች ግንኙነታቸዉን ያጠናክራሉ ያሏቸዉን ዉሎች ተፈራርመዋል።የሁለቱ ሐገራት ግንኙነት ተቋርጦ የነበረዉ የኢትዮጵያ መንግሥት፥ ቀጠር ኤርትራንና ኤርትራ ዉስጥ የሚገኙ የኢትዮጵያ አማፂያንን ትረዳለች በማለት በመወንጀሉ ነበር።ነጋሽ መሐመድ ዝር ዝር ዘገባ አለዉ።
የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር አቶ ሐይለማርያም ደሳለኝ፥ የቀጠሩን አቻቸዉን ሼኽ ሐማድ ቢን ጃሲም አ-ሳኒን ካነጋገሩ በሕዋላ፥ የፈረንሳዩ ዜና አገልግሎት አዣንስ ፍራንስ ፕረስ እንደጠቀሰዉ፥ «ግንኙነታችንን በመተማመንና በቅን ልቦና ማጠናከር ከምንችልበት ጊዜ ደርሰናል» ብለዋል።
ግንኙነቱ ከ«መተማማን» እና «ከቅን ልቦና» የደረሰዉ ለግንኙነቱ መበላሸት ምክንያት የሆነዉ ጠብ እንዴት ተወገዶ ነዉ? የሚል ጥያቄ ማስነሳቱ አልቀረም።የኢትዮጵያ ዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ያለፈዉን ልዩነት «የድልድይ በታች ዉሐ» በማለት በዲፕሎማሲዉ የግድምድሞሽ ቋንቋ ዘለሉት።
ግንኙነቱን ቀድማ ያቋረጠችዉ ኢትዮጵያ ነበረች።በሁለት ሺሕ ግድም።ለግንኙነቱ መቋረጥ የያኔዉ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊ የሰጡት ምክንያት ትንሺቱ ሐብታም አረባዊት ሐገር የኢትዮጵያን «ጠላት» ኤርትራንና በኤርትራ የሚደገፉ አማፂያንን ትረዳለች የሚል ነበር።
ግንኙነቱ አሁን እንዳዲስ የቀጠለዉ ቀጠር የኢትዮጵያ «ጠላቶች» ለሚባሉት የምትሰጠዉን ድጋፍ በማቋረጧ ይሆን? ISS በሚል የእንግሊዝኛ ምሕፃረ ቃል የሚጠራዉ የፀጥታ ጥናት ተቋም የፖለቲካ ተንታኝ አቶ ብሩክ መስፍን «ቆይተን እንይ» አይነት ነዉ መልሳቸዉ።ያም ሆኖ ሁለቱ ሐገራት ግንኙነታቸዉን መቀጠላቸዉ የፖለቲካ አጥኚ ብሩክ መስፍን እንደሚሉት በብዙ ጎኑ ጥሩ ነዉ።
የሁለቱ ሐገራት ሚንስትሮች ትናንትናዉኑ የተለያዩ ስምምነቶችን ተፈራርመዋል።አምባሳደር ዲና እንደሚሉት የስምምነቱ ዓይነት ብዙ፥ ዝርዝሩ ሰፊ ነዉ።ሁለቱ ሐገሮች መቀራረባቸዉ የፖለቲካ ተንታኝ ብሩክ መስፍን እንደሚሉት በተለይ ቀጠር ካላት የማስታረቅና የመሸምገል ሚና አኳያ ሲታይ ለኢትዮጵያም ለአካባቢዉም ጠቃሚ ነዉ።
አምባሳደር ዲና እንዳስታወቁት ቀጠር አዲስ ዉስጥ የኤምባሲ ፅፈት ቤት ከፍታለች።ኢትዮጵያም በሚቀጥለዉ ወር ኤምባሲ ፅፈት ቤት ለመክፈት አቅዳለች።
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ