የኢራን የአቶም መረሃ-ግብር ስምምነት
እሑድ፣ ኅዳር 15 2006
ድርድሩን ሲመሩ የነበሩት፤ በፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ዉስጥ ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣን ያላቸዉ አምስቱ ሐያላን ሀገራትና የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጊዶ ቬስተርቬለ እንዲሁም፤ የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ካትሪን አሽተን ገልፀዋል። ከጥቅምት ወር ወዲህ ለሶስተኛ ጊዜ በተካሄደዉ በዚሁ ንግግር ኢራን ዩራንየም በከፍተኛ ደረጃ ከማብላላት እንድትቆጠብ በምትኩም ምዕራቡ ዓለም የጣለባትን የኤኮኖሚ ማዕቀብ ለጊዜው እንዲያላላ የታሰበ እንደነበር ተመልክቷል። ከሁለት ሳምንት በፊት ኢራንና አምስቱ የተመድ ፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት አባላት እንዲሁም ጀርመን ባካሄዱት ንግግር ኢራን 20 ከመቶ የደረሰውን ዩራንየም የማብላላት ደረጃዋን ወደ 3.5 በመቶ ዝቅ እንድታደርግ በሚጠይቀው ውል መስማማት ተስኗቸው መለያየታቸዉ ይታወሳል። በዉይይቱ አኳያ ከኢራን ወገን እንደተገለፀዉ፤ ሀገሪቱ ከምታካሂደዉ የአቶም መረሃ-ግብር አንዱን ክፍል ታቆማለች። ለዚህም በኢራን ላይ የተጣለዉ ዓለም አቀፍ ማዕቀብ ይነሳል ተብሏል። እንደ ኢራኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሃመድ ዣዋድ ሻሪፍ ትንተና በተደረሰዉ ስምምነት ላይ፤ ኢራን የምታመርተው ፕሉቶንየም ተቀባይነት ያገኘ ግን፤ ሀገሪቱ በሚቀጥሉት ስድስት ወራቶች የምታብላላዉ የፕሉቶንየም መጠን ከአምስት በመቶ በልጦ መገኘት የለበትም። የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከዋይት ሃዉስ በሰጡት መግለጫ፤ በአቶም ጉዳይ የተነሳን ጭቅጭቅ እስከ መጨረሻዉ ለማወገድ፤ ስምምነቱ እጅግ ወሳኝ እርምጃ ነዉ ሲሉ ገልጸዋል። ከአደራዳሪዎቹ መካከል አንዱ የሆኑት የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጊዶ ቬስተርቬለ በበኩላቸዉ፤ ኢራን የአቶም መሣርያን ተጠቃሚ እንዳትሆን፤ ወሳኝ ከሆነዉ የዓላማ መዳረሻ ላይ ተቃርበናል ብለዋል።
የዓለም ኃያላን መንግሥታት፤ አራን በሚገኘው ማብላያ የሚመረተው ፕሉቶንየም እንዲሁም 20 በመቶ ዩራንየም ለኒዩክልየር ጦር መሣሪያዎች ማምረቻነት ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላል የሚል ስጋት ያላቸዉ ሲሆን፤ምዕራባዉያን ሀገራት፤ ኢራንኑክሌር ቦምብ ትሰራበታለች ብለዉ የሚጠረጥሩትን የኑክሌር መርሐ ግብሯን ባለማቋረጧ ተደጋጋሚ ማዕቀብ ጥለዉባት ቆይተዋል። የቴህራን መንግሥት በበኩሉ ወቀሳውን ሀሰት በማለት፣ የአቶም መረሃ -ግብሩ ለሠላማዊ የኃይል ምንጭ ተግባር ጥቅም ላይ እንደሚያዉል በተደጋጋሚ ሲገልፅ መቆየቱ ይታወቃል።
አዜብ ታደሰ
ልደት አበበ