1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍራሽ ግብረ-ኃይል እና የነዋሪዎች ግጭት በአዲስ አበባ

Merga Yonas Bulaሐሙስ፣ ሰኔ 23 2008

በአፍራሽ ግብረሃይል እና በላፊቶ ክፍለከተማ ነዋሪዎች መካከል ትናንት በተፈጠረ ግጭት አንድ የወረዳ ስራ አስፈፃሚ፣ ሁለት ፖሊሶች እና አንድ የአከባቢዉ ነዋሪ ሕይወት ማለፉ ተዘግቧል።

https://p.dw.com/p/1JGvu
Addis Ababa (Äthiopien)
ምስል picture alliance/landov

[No title]

የግጭቱ ትክክለኛ ምክንያት በግልፅ አልታወቀም።አንዳዶች እንደሚሉት ግን መንስኤዉ መንግስት ከ30,000 በላይ ቤቶችን <<ህገወጥ ናቸዉ>> በሚል ነዋሪዎቹ በሶስት ቀናት ዉስጥ እንድያፈርሱ በማዘዙ ነዉ።

የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር እንደሚለዉ በከተማይቱ የመሬት መረጃ ስረዓት ለመዘርጋት እና ለማስተዳደር አዲስ ምዝገባ ጀምሯል።በዚሕም መሠረት እስከ 1997 ሰነድ ሳይኖራቸዉ መሬት የያዙ ከ40,000 በላይ ነዋሪዎችን መዝግቦ ወደ ስርዓቱ ለማስገባት አስተዳደሩ እየሰራ መሆኑን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሸን ጉዳዮች ቢሮ ሐላፊ ወዜሮ ዳግማዊት ሞገስ ለዶቼ ቬሌ ገልፀዋል። በቅርቡ በቦሌ ክፍለ ከተማ የተከሰተዉ እና አሁን ነፋስ ስልክ ላፍቶ የተፈጠረዉ ግጭት አስተዳደሩ ህገወጥ ግንባታ መሆኑን ካረጋገጠ በኋላ ነዉ ሲሉ አብራርተዋል።


በፌስ ቡክ ገፃችን አስተያየት የሰጡ ወገኖች መንግሥት ወይም የአዲስ አበባ መስተዳድር አሁን <<ህገወጥ>> ያላቸዉ ቤቶች ሲገነቡ ለምን ዝም ብሎ ተመለከተ? ወይስ የት ነበር? በማለት ይጠይቃሉ።ጉዳዩስ ወደ ከፋ ግጭት ሳይሸጋገር በሰለማዊ መንገድ መፍታት ለምን አልተቻለም ብለውም የሚጠይቁ አሉ።

አስተያየት ሰጭዎቹ እንደሚሉት መንግስት አሁን መሬቱን ለራሱ ጥቅም ሊያዉል ፈልጎት እንጂ ማህበረሰቡን ሊጠቅም አይደለም በማለት ይከራከራሉ። ሌሎች ደግሞ «ነዋሪዎቹ በዚህ ከባድ ክረምት የት ይፍሰሱ?»። መንግስት ህዝብ አይደለም እንዴ። ለማን ይሰራል?>> ሲሉ ከጠየቁ በኋላ <<የሰው ህይወት መጥፋቱ አሳዛኝ ነው። ችግሩን በውይይት መቅረፍ ቢችሉ መልካም ነበር።>> በማለት አስተያየታቸዉን ሰንዝረዋል።

መርጋ ዮናስ

ነጋሽ መሃመድ