የአፍሪቃ አንድነት እና የጋዜጠኞቹ ትዉስታ
ማክሰኞ፣ ግንቦት 20 2005
ከአፄ ሐይለ ሥላሴ-እስከ ክዋሚ ንኩሩማሕ፥ ከሁፌት ቧኚ እስከ ገማል አብድ ናስር የነበሩ ሰላሳ-ሁለት የአፍሪቃ መሪዎች የዛሬ-ሐምሳ ዓመት አዲስ አበባ ላይ ታሪክ ከሰሩ፥ ሲሰሩ-እሱ ታሪኩን ይዘግብ ነበር።
ጋዜጠኛ ፀጋዬ ታደሰ።ይኸኛዉ ሠሞኑን አዲስ አበባ ላይ የሆነ እና የሚሆነዉን የአፍሪቃን ታሪክ በእርግጥ ይዘግባል።ያኔ ግን ጋዜጠኛ አልነበረም።ያኔ አዲስ አበባ የተደረገዉ ሲደረግ ግን እንደ አስተርጓሚ በቅርብ አይቶታል።
ጌታቸዉ ተድላ ሐይለ ጊዮርጊስ። የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ሐምሳኛ ዓመት መነሻ፥ የታሪክ ነጋሪዎቹ የታሪክ ትዉስታ ማጣቀሻ ትዝብታቸዉ መድረሻችን ነዉ ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ። በአንጋፋ እድሜዉ ላይ የጋዜጠኝነት በጣሙን የዜና-ሰዉነት ምግባሩ፥ አወዛጋቢዉን፥ ለአደጋ የሚያጋልጠዉን፥ ፈታኝ ሙያ የተወጣበት ብልሐቱ ሲታከልበት አንቱ-አለማለት ሲበዛ ከብዶኝ ነበር።
ገላገለኝ። ክበደቱ እንዲቀለኝ ጋሼን እያስቀደምኩ፥ አንተን አስከትዬ በሱ ቋንቋ-እየዘረጠጥኩት ዉይይታችንን ቀጠልን። መጀመሪያ ፀጋዬ ነበር። ፀጋዬም መምሕር ሆነ።
መምሕሩም ጋዜጠኛ ሆነ። እዚያዉ አዲስ አበባ ተወልዶ-ያደገዉ ጌታቸዉ ተድላ ፀጋዬ ታደሰን እንደ ጋዜጣኛ ከሩቅ እንደሚከተለዉ፥ እድል፥ አጋጣሚ፥ ወይም የሕይወት ጉዞ እዉቀት ካለቸዉ ያዉቁ ነበር ካልተባለ በስተቀር አስከታይም፥ ተከታይም፥ የሁለቱም ወላጅ፥ ወዳጅ ዘመዶች ማናቸዉም አያዉቁትም።
ፀጋዬ ኢትዮጵያን ሔራልድ ላይ የእንግሊዝኛዉን እየበጠሰ ሲቀጥል፥-ጌታቸዉ ፈረንሳይኛዉን ይሰልቀዉ ገባ፥-
በ1958 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) የደቡብ አፍሪቃን የጠቅላይ ሚንስትርነት ሥልጣን የያዙት አክራሪዉ ነጭ ዘረኛ ፖለቲከኛ ሔድሪክ ቬርቮርድ የጥቁር መብት ተሟጋቾችን በተለይም የደቡብ አፍሪቃ የአፍሪቃዉያን ብሔራዊ ምክር ቤት (ANC) መሪዎችን ማስገደል፥-ማሳሰር ፣ማሰደዱን የጀመሩት ሥልጣን በያዙ ማግሥት ነበር።
ሕዳር 1962 እዉቁ የመብት እኩልነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ከዘረኛዉ የቬርቮርድ መንግሥት እጅ ወደቁ። ጠቅላይ ሚንስትር ቬርቮድ ማንዴላን በአመፅ ቀስቃሽና አሳዳሚነት ወንጀል አምስት ዓመት እስራት ባስፈረዱባቸዉ ማግሥት ሐገራቸዉን ወደፊት የሚመሠረተዉ የአፍሪቃ ማሕበር አባል ለማድረግ ረግጠዉ ከሚገዙት ጥቅር ሕዝብ የቀመቱን ገንዘብ-ያንዠቀዥቁት ያዙ።
የሞንሮቪያና የካዛብላንካ ቡድን በሚል ለሁለት ከተገመሱት የአፍሪቃ መሪዎች ጥቁሮቹን ለሚረግጠዉ ለቬርቮርድ መንግሥት ከጥቁር መሪዎች ተባባሪ ማግኘቱ ዛሬ ያስግርም-ይሆናል። ግን-እዉነት ነዉ። እዉነቱ ለወጣቱ ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ የብዙ መጀመሪያዎች ሆነ። ለመጀመሪያ ጊዜ ከኢትዮጵያ ዉጪ ተጓዘ። ለመጀመሪያ ጊዜ ከዓለም ጋዜጠኞች ጋር ተዋወቀ፥--ለመጀመሪያ ጊዜ ስዩመ እግዚአብሔር ንጉሰ ነገስት ዘ-ኢትዮጵያ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ በአደባባይ ያረጁ የሚረሱ (ሴናይል) መሪ እየተባሉ ሲወረፉ ሰማ። አልታገሰም። ለመጀሪያ ጊዜ---እሱ ይቀጥል----
በዚያዉ ሰሞን ነዉ። የአፍሪቃ መሪዎች አንድም የሞንሮቪያ እና የካሳብላንካ ቡድን እንዳሉ እሁለት እንደተከፈሉ ለመቅረት፥ አለያም ከልዩነታቸዉ ጋር እንድ እንደምታደርጋቸዉ አሐጉር-አንድ ሆነዉ የጋራ ማሕመር ለመመስረት የአዲስ አበባ ጉባኤያቸዉን ቀን ሲያሰሉ፥እሱ ለመጀመሪያ ጊዜ ደሞዝ ለመብላት፥ ለመጀመሪያ ጊዜ ዉጪ ለመሔድ-አመለከተ። ለመጀመሪያ ጊዜ፥----ጌታቸዉ
አዲስ አበባ- እና እንግዶችዋ፥በአዲስ አበቦች አይን----
ጉባኤተኞች፥-ታሪክ ሠሪዎቹና ታሪክ ነጋሪዉ፥-ሰላሳ-ሁለቱ የአፍሪቃ መሪዎች ልዩነታቸዉን አቻችለዉ የማሕበራቸዉን መተዳደሪያ ደንብ ፈረሙ። ለአፍሪቃ አዲስ ታሪክ፥ አዲስ ተስፋ ፈነጠቀ። የብሪታንያዉ ግዙፍ ማሠራጪያ ጣቢያ ቢቢሲ ግን የማሕበሩን መመስረት «የአፍሪቃ መንግሥታት በነጭ አጋዛዝ አንፃር ተባባሩ» በሚል ርዕሥ ዘገበዉ።እሱስ?
ፀጋዬ ኢትዮጵያን ሔራልድ ላይ አፍሪቃን እንኳን ደስ አለሽ ካለ በሕዋላ-እንደ አፍሪቃ ብዙ አይቷል።ሔራልድን ለቅቆ፥ የግል ሥራ ጀምሮ ነበር። የጋዜጠኝነቱ ቆሌ ግን እንደገና ጠራዉ። በኢትዮጵያ የሮይተርስ ወኪልነት ሆነ።
ጌታቸዉ ፈረንሳይ ተምሮ፥ ወደ ሐገሩ ተመልሶ፥ በግሉም፥ በተለያዩ መስሪያ ቤቶችም ሲሰራ ቆይቶ ኋላ-ጋዜጠኛ ሆኗል። አሁን በአዲስ አበባ የዶቸ ቬለ ዘጋቢ ሆኖ የቀድሞዉ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ያሁንኑ የአፍሪቃ ሕብረት እንቅስቃሴ ይዘግባል።
ፀጋዬ መጀመሪያ የሄደባት ሐገር ኮትዲቯር ወይም አይቮሪኮስት በእርስ በርስ ጦርነት፥ በፈረንሳይ ጣልቃ ገብ ጦርና በቀድሞ መሪዋ ታማኞች ዉጊያ ባለቁ ዜጎቿን ሐዘን እንደተቆራመደች ነዉ። የወደመ ሐብት ንብሯትን ጠግና አላበቃችም። ጌታቸዉ ለመጀመሪያ ጊዜ ያያቸዉ መሪ የሞዲይቦ ኬይታ ሐገር ማሊ በመፈንቅለ መንግሥት፥ በአክራሪዎች፥ በቱአሬግ ደፈጣ ተዋጊዎች፥በፈረንሳይ ጦርና በቻድ ተባባሪዎቹ ዉጊያ እየወደመች ነዉ። ጌታቸዉ መጀመሪያ ያያት ሐገር የዛሬዋ ኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ የዛሬ-ሐምሳ ዓመት የርስ በርስ ጦርነት ላይ ነበረች። ዛሬም ጦርነት ላይ ነች።
የሐምሳ ዓመቱ አንጋፋ ማሕበር አባላት ዛሬ ሐምሳ-አራት ደርሰዋል። ሁሉም ሐገራት ከቀጥታ ቅኝ አገዛዝ እና ከነጭ ዘረኞች ጮቆና ነፃ ወጥተዋል። አፍሪቃዉያን የእዉነተኛ ነፃነት ባለቤቶች፥ የሠላም፥ የዲሞክራሲ፥ የእኩልነት፥ የፍትሕ ባለመብቶች፥የሐብታቸዉ እኩል ተጠቃሚዎች የሚሆኑበት ዘመን ግን-ዛሬም በሐምሳኛ ዓመቱ ሩቅ መምሰሉ እንጂ ቁጭቱ። ፀጋዬና ጌታቸዉን አመሠግናለሁ፥ ነጋሽ መሐመድ ቸር ያሰማን።
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሰ