የአፍሪቃ ኅብረት በመሪዎች ጉባኤ አዲስ ሊቀመንበር ሾመ
ቅዳሜ፣ ጥር 21 2008አዲስ የተመረጡት ሊቀመንበር ባደረጉት ንግግርም በአህጉሩ ዙሪያ ያሉት ግጭቶች ማቆም እንዳለባቸው ገልጸው፦ « በዲፕሎማሲያዊ መንገድም ይሁን በኃይል በዘመናችን የተከሰተውን አሳዛኝ ሁኔታ ማብቃት ይኖርብናል ብለዋል። የ63 አመቱ የቻድ ፕሬዚዳንት ኢድሪስ ዴቢ የ91 ዓመቱን የዝምባብዌ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ተክተው ነው የተመረጡት። ያለፈው ዓመት ሊቀመንበር የነበሩት ሙጋቤ ለአዲሱ ሊቀመንበር እንኳን ደስ አልዎት ብለው፤ ለማንኛውም ድጋፍ ከጎናቸው እንደሆኑ ገልጸዋል። የአፍሪቃ ህብረት ሊቀመንበር በየዓመቱ ከመሪዎቹ መካከል ይመረጣል። ሌላው የአፍሪቃ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ትኩረት የቡሩንዲ የጸጥታ ጉዳይ ነው። የአፍሪቃ ህብረት የፀጥታው ካውንስል፣ የጉባኤው ተካፋይ የሀገር መሪዎች እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች የቡሩንዲን ግጭት ለማብረድ ህብረቱ ለመላክ ስላቀደው ሰላም አስከባሪ ኃይል ከጉባኤው መክፈቻ በፊት ትናንት ዓርብ አንስተው ተወያይተዋል። ህብረቱ ወደ 5000 የሚጠጉ አባላትን ያቀፈ ሰላም አስከባሪ ኃይል ለመላክ የደረሰውን ውሳኔ የቡሩንዲ መንግሥት አሁንም አልተቀበለውም። የቡሩንዲን የፀጥታ ጉዳይ አስመልክቶ በዚህ ጉባኤ ህብረቱ ወታደሮቹን ወደ ቡሩንዲ ለማዝመት ከወሰነ፤ ካለ አንድ አባል ሀገር ፍቃድ ህብረቱ ሰላም አስከባሪ ጓድ ሲያዘምት የመጀመሪያው ይሆናል።
ልደት አበበ
ማንተጋፍቶት ስለሺ