የአፍሪቃ ምጣኔ ሐብት
ሐሙስ፣ ግንቦት 2 2004
አዲስ አበባ የተሰበሰቡት የአፍሪቃ የምጣኔ ሐብት አዋቂዎችና ባለሙያዎች የአፍሪቃ የምጣኔ ሐብት እድገትንና እድገቱ የሚኖረዉን ፋይዳ አንስተዉ ተወያተዋል።ተሰብሳቢዎቹ የአፍሪቃ ምጣኔ ሐብት እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በ2050 ሥለሚደርስበት ደረጃና ከዕድገቱ ሕዝቡ ሥለሚጠቀምበት ሁኔታ ያላቸዉን ምክርና አስተያየት ሰጥተዋል።ተሰብሳቢዎቹ እንዳሉት እስካሁን አፍሪቃ ዉስጥ ከታየዉ የምጣኔ ሐብት እድገትም ሆነ ከአፍሪቃ የተፈጥሮ ሐብት የአፍሪቃ ሕዝብ ተጠቃሚ አልሆነም።ታደሰ እንግዳዉ ከአዲስ አበባ ዝር ዝር ዘገባ አለዉ።
በተያያዘ ዘገባ የቀድሞው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ ኮፊ አናን፣ የአፍሪቃ መንግስታት የአህጉሩ ዕድገት ቀጣይነት ያለው እንዲሆን ወጣቱን ትውልድ ማስተማር ይኖርባቸዋል አሉ። አናን ፤ አዲስ አበባ ውስጥ በመካሄድ ላይ ባለው የዓለም የኤኮኖሚ መድረክ ፣ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ነው፣ ይህን ማሳሰቢያ ያቀረቡት። 60 ከመቶ በላይ የሚሆነው የአፍሪቃ ህዝብ ፣ ዕድሜው ከ 30 ዓመት በታች ነው። በዕድገት ለመራመድ፤ አናን ፣ አፍሪቃውያን መንግሥታት፣ ለህዝባቸው ብልጽግናን ማስገኘት በሚያስችሉ ተግባራት ላይ ማትኮር ይገባቸዋል፤ የህዝብን ኑሮ የሚያሻሽሉ የማኅበራዊና የኤኮኖሚ መርኆዎችንም መቀየስ ይኖርባቸዋል ብለዋል። ነገ በሚደመደመው የ 3 ቀናት ጉባዔ፤ በመካፈል ላይ ካሉት ከ 700 በላይ ተሳታፊዎች መካከል፣ 8 የአፍሪቃ መሪዎችና የቀድሞው የብሪታንያ ጠ/ሚንስትር ጎርደን ብራውን ይገኙበታል።
ታደሰ እንግዳዉ
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ