1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ ሕብረት ጦር አሸባብ ላይ አዲስ ዘመቻ ከፈተ

ማክሰኞ፣ ሐምሌ 14 2007

የአፍሪቃ ሕብረት ጦር የሶማሊያው ኧልሸባብ ላይ አዲስ ጥቃት መክፈቱን ዛሬ ገለፀ። የህብረቱ ጦር ከአል-ቃይዳ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው የሚነገርላቸው የአሸባብ ታጣቂዎችን ከገጠራማ ደቡብ ሶማሊያ ለማስለቀቅ ዝቷል።

https://p.dw.com/p/1G1ME
AMISOM - Soldaten in Somalia
ምስል picture alliance/dpa/Jones

አሚሶም በመባል የሚታወቀው የአፍሪቃ ሕብረት የሶማሊያ ተልእኮ እንዳስታወቀው ከመዲና ሞቃድሾ በስተ ደቡብ በኩል፤ ቤይ እና ጌዶ በተባሉት አካባቢዎች የህብረቱ ጦር ከሶማሊያ የመንግሥት ጦር ጋር በመተባበር አዲሱን የጥቃት ዘመቻ ከፍቷል። አሚሶም በሰጠው መግለጫ በተቀሩት የሶማሊያ አከባቢዎችም ሰላም እና መረጋጋት እስኪሰፍን ድረስ የጦሩ ርምጃ ይቀጥላል ብሏል። ባለሥልጣናት እና የዓይን እማኞች የኧልሸባብ ጠንካራ ይዞታ እንደሆኑ በሚነገርላቸው ዲንሶር እና ባርዳሬ ከባድ ውጊያ እንደተቀሰቀሰ ገልጠዋል።

Infografik AMISOM Mission der Afrikanischen Union in Somalia

ዘመቻውን በሚመሩት የኢትዮጵያ ወታደሮች የተሽከርካሪ አጀብ ላይም መንገድ ዳር በተጠመደ ፈንጂ ጥቃት ደርሷል ሲሉ እማኞቹ መናገራቸውን የፈረንሣይን ዜና አገልግሎት ዘግቧል። ይህ አዲስ የማጥቃት ዘመቻ የጀመረው የኬንያ መንግሥት አንድ ሰው አልባ የዩናይትድ ስቴትስ አይሮፕላን በዚሁ አካባቢ በርካታ የጦር አመራርን ጨምሮ ቢያንስ 30 የአሸባብ ወታደሮችን መግደሉን ይፋ ካደረገ ከቀናት በኋላ ነው።

የአሸባብ ቡድን መሪ፤ አህመድ ዲሪዬ የሙስሊሞች ኢድ አል ፈጥር በዓል በተከበረበት ዓርብ ዕለት እንዳመለከተው ቡድኑ ከሶማሊያ ውጪ በተለይም በኬንያ የሚወስደውን ርምጃ አጠናክሮ ይቀጥላል።

ልደት አበበ

ማንተጋፍቶት ስለሺ