የአፍሪቃ ሕብረት ጉባኤና ልዩነቱ
ዓርብ፣ ሐምሌ 6 2004
12 07 12
19ኛዉ የአፍሪቃ ሕብረት መደበኛ ጉባኤ ባለፈዉ ሰኞ በአምባሳደሮች ደረጃ ተጀምሯል።ያሁኑን ጉባኤ ማስተናገድ የነበረባት ማላዊ ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት እንዲታሰሩ የበየነባቸዉን የሰሜን ሱዳኑ ፕሬዝዳት ዑመር ሐሰን አልበሽርን አልጋብዝም በማለቷ ጉባኤዉ ገና ሳይጀመር ዉዝግብ አጥልቶበት ነበር።የጉባኤዉ ሥፍራ ከሊሉንግዌ ወደ አዲስ አበባ ከተቀየረ በሕዋላ የማላዊ ፕሬዝዳት ጆይስ ባንዳ በጉባኤዉ ላለመካፈል ወስነዋል።የጉባኤ ጭብጥ የአፍሪቃን የርስ በርስ ንግድ ማጠናቀር የሚል ነዉ። ይሁንና ሉድገር ሻዶምስኪ እንደሚለዉ ሕብረቱን የገጠመዉ ዉዝግብና የአባል ሐገራት ቀዉስ የጉባኤዉ ዋና ጭብጥ ለማጎል በቂ ሰበብ ነዉ።የሉድገርን ዘገባ ነጋሽ መሐመድ ባጭሩ አጠናቅሮታል።
የፊታችን ሰኞ የሚጠናቀቀዉ ጉባኤ፥ ሕብረቱ የቀድሞዉን ደካማ የሚባለዉን የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን ከተካበት አስረኛ አመት ጋር ተገጣጥሟል።ሕብረቱም ቢሆን ባለፉት አስር አመታት ያከናወናቸዉ ተግባራት ጥንካሬዉን መስካሪ አይደሉም።አሁንም በዉዝግብ እንደተዋጠ ነዉ።
ዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች መዳኛ ፍርድ ቤት በሰሜን ሱዳኑ ፕሬዝዳት በዑመር ሐሰን አል-በሽር ላይ የቆረጠዉ የእስራት ዋራንት-በርግጥ የሕብረቱ ጉባኤ የመነጋገሪያ ርዕሥ አይደለም።አባል ሐገራትን ከሚያወዛግቡ ጉዳዮች ግን አንዱ ነዉ።ሕብረቱ ከፍርድ ቤቱ ጋር እንደማይተባበር ከሁለት አመት በፊት ወስኗል።
የፍርድ ቤቱን የምሥረታ ደንብ የተቀበሉ ብዙ የአፍሪቃ ሐገራት ግን ዉሳኔዉን አልተቀበሉትም። ሌሎች አስራ-አንድ ሐገራት ደግሞ በፊርማቸዉ አላፀደቁትም።
የሕብረቱን ኮሚሽን ፕሬዝዳት መምረጡ ሌላዉ የዉዝግብ ሰበብ ነዉ።ባለፈዉ ጥር ተሰይሞ የነበረዉ ጉባኤ በሥልጣን ላይ ካሉት ከዤን ፒንግ እና ከደቡብ አፍሪቃዋ የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ከንኮሳዛና ድላሚኒ-ዙማ አንዳቸዉን መምረጥ ተስኖት ላሁኑ ስብሰባ በይደር ነበር የተወዉ።
አባል ሐገራት አለመስማማታቸዉን አንዳዶች የእንግሊዝኛና የፈረንሳይኛ ተናጋሪ ሐገራት ልዩነት አድርገዉ ያዩታል።የዓለም አቀፉ የፀጥታ ጥናት ተቋም ISS አጥኚ ኢዴ ኦኬኬ እንዲሕ አይነቱን አስተያየት አሳሳች ይሉታል።
«ልዩነቱን የአንግሎ ፎንና የፍራንኮ ፎን ተናጋሪ ሐገራት ልዩነት አድርጎ መናገር አሳሳች ይመስለኛል። የአንግሎ ፎንና የፍራንኮ ፎን ልዩነት አይደለም።ይልቅዬ በአካባቢያዊ ትላልቅ ሐገራት መካከል ያለ ልዩነት ነዉ።የጥቅም ግጭት።»
የአፍሪቃ ሕብረት የኮሚሽኑን የፕሬዝዳትነት ሥልጣንን የአናሳዎቹ ሐገራት ዜጋ መያዝ አለበት የሚል ያልተፃፈ ሕግ አለዉ።ደቡብ አፍሪቃ የራሷን እጩ ስታቀርብ ይሕን ሕግ አፍርሳለች። ምክንያቷ ሕብረቱ ሊቢያ የደረሰዉን አይነት ቀዉስ ለማስወገድ ጠንካራ መሪ ያስፈልገዋል የሚል ነዉ።
የጊኒ ቢሳዉና የማሊ ፖለቲካዊ ቀዉስ የጉባዉ ትላልቅ ርዕሶቹ ናቸዉ።የምዕራብ አፍሪቃ የምጣኔ ሐብት ማሕበረሰብ ECOWAS የማሊ ሙስሊም አማፂያንን የሚወጋ ጦር ለማዝመት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ይሁንታ እየጠበቀ ነዉ።ድርጅቱ ግን እስካሁን አልፈቀደም።ጊጋ በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ የጀርመኑ ጥናንት ተቋም የአፍሪቃ ጉዳይ አጥኚ አንድሪያስ ሜሕለር እንደሚሉት አለም አቀፉ ድርጅት ከመወሰኑ በፊት ብዙ ጉዳዮችን ማጤን አለበት።
«እንደሚመስለኝ መጀመሪያ ተጨባጭ እቅድ ሊኖር ይገባል።ምን መደረግ እንደለበት፥ምን ጦር መዝመት እንደሚገባዉ፥ የአለማዉ ምንነትና ፖለቲካዊ ግቡ በግልፅ መታወቅ አለበት።እነዚሕ እስካሁን ግልፅ የሆኑ አይመስለኝም።ኤኮዋስ ትንሽ ፈንጠር ብሎ ሔዶ ሌሎቹን ከጀርባዉ እየጎተተ ነዉ።»
የሶማሊያ ዉጊያና ምሥቅልቅል፥ የሱዳኖች ዉዝግብና ግጭትም የጉባኤዉን ትኩረት የሚሹ ናቸዉ።ሶማሊያ ከትርምሷ ጋር የሽግግር መንግሥቷ ዘመነ-ሥልጣን የፊታችን ነሐሴ አጋማሽ ያበቃል።እንዴት ትቀጥለች።እንደገና አንድሪያስ ሜሕለር፥-
«አዎ-ግልፅ ነዉ።አሸባብ እንደፊቱ ጠንካራ አይደለም።አጠቃላይ ሐገሪቱን የሚቆጣጠር ግን ማንም የለም።ሥለዚሕ የአፍሪቃ ሕብረት የግድ ሁነኛ እርምጃ መዉሰድ አለበት።ሕብረቱ ምናልባት ይሕን አለ ለማለት ያያሕል ያደርገዉ ይሆናል።በተጨባጭ ግን ትንሽ ነዉ የተደረገዉ።እና በመጨረሻ የተሠራዉ ተሠራ ለመባል ያሕል ይሆንና የሚለወጠዉ ምንም ወይም ትንሽ ይሆናል።»
በነዳጅ ዘይት ሐብት፥ በድንበር፥ ተቃዋሚዎችን በመርዳት የሚወዛገቡት ሁለቱ ሱዳኖች እዚያዉ አዲስ አበባ ዉስጥ ለተከታታይ ወራት ቢደራደሩም እስካሁን ተጨባጭ መፍትሔ ላይ አልደረሱም።ጉባኤዉ ይወስናል ተብሎ ይጠበቃል።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ