የአውሮፓ እግር ኳስ ሻምፒዮና
ዓርብ፣ ግንቦት 10 2004አልቋል፣ እንዲያውም በመጨረሻ አንዳንድ ሰዎች ፣ አንድ ትኬት ፣ እስከ 15,000 ዩውሮ መሸጣቸው ወይም መግዛታቸው ተንግሮአል። የዋንጫው ባለቤት ማን ይሆን?
ሁሉም ፤ የድል ባለቤት ለመሆን እንደቋመጡ ናቸው። የጀርመኑ ታዋቂ የእግር ኳስ ክለብ ባየርን ሙዑንሸንና ፤ የእንግሊዙ ቸልሲ! ጨዋታውን ፤ ነገ ጊዜው ደርሶ ለማየት ኳስ አፍቃሪዎች በእጅጉ ጓጉተዋል። የእስፖርት ጋዜጠኞችም በየዘገባቸው የውድድሩን መንፈስ በማሟሟቅ ላይ ናቸው። የምዕተ-ዓመቱ ዐቢይ ጨዋታ እያሉም ከወዲሁ ማዳነቅ ይዘዋል። በጀርመን የአንደኛ ምድብ ክለቦች ፤ የሻምፒዮናውንና የጥሎ ማለፉን ሀገራዊ ዋንጫ በመሰብሰብ ክብረ ወሰን እንደያዘ የሚገኘው ባየርን ሙዑንሸን፤ በራሱ ሜዳ ሙዑንሸን ላይ የሚጋጠም በመሆኑ ፤ አመቺ ሁኔታ ሳይፈጠርለት እንዳልቀረ የብዙዎች ግምት ነው። ይሁንና የኳስ ግጥሚያ ጉዳይ ያልታሰበ ውጤት ስለሚመዘገብበት ከጅምሩ እስከፍጻሜው ደርሶ ለማየት መጓጓቱ ያለ ነገር ነው። ባየርን ሙዑንሸን ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በርሊን ላይ በተካሄደው የጥሎ ማለፍ ዋንጫ የፍጻሜ ውድድር፣ በቦሩሲያ ዶርትሙንድ 5-2 ተረትቶ ፣ ሁሉንም ካጣ ወዲህ፣ ያለው ብቸኛ አማራጭና ዕድል ይኸው የነገው የአውሮፓ ሻምፒዮና የፍጻሜ ውድድር ነው። ያለፈውን ሳምንት አይሸነፉ- ሽንፈት በቁጭት በማሰብም ነው ፣ የባየርን የፊት አጥቂ ፣ ኔደርላንዳዊው አርየን ሮበን፣ ትናንት፣ የከተማይቱ ህዝብ በመላ ከቡድኑ ጎን እንዲቆም ከመመጻንም ሌላ እንዲህ ያለው---
«ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ መሸነፋችን ብቻ ሳይሆን፤ ፤ የዘንድሮውን የአገር ውስጥ የሻምፒዮና ዋንጫም አላገኘንም ። የቀረን አንድ ዕድል ብቻ ነው። ይህ እንግዲህ ምናልባት ለነገው ቅዳሜ ጨዋታ ፣ በእልህ የሚያበረታታ ሊሆን ይችላል ። »
የባየርን ሙዑንሸን ቡድን የአስተዳደር ክፍል ተጠሪ ካርል ሃይንትዝ ሩመኒገ ከ F C Chelsea የሚካሄደውን ግጥሚያ በናፍቆት እንደሚጠብቅ ከመግለጹም ፤ የክለቡ ተጫዋቾች፤ መረበሽም መርበትበትም ቢያጋጥማቸው የሚያስገርም እንዳልሆነ ነው የተናገረው። እንደ አርየን ሮበን ሌላው የባየርን ሙዑንሸን የፊት አጥቂ ተጫዋች ብራዚላዊው ራፊኛ ፣ እንዲህ ብሏል።
«ለዚህ የአውሮፓ ሻምፒዮና የፍጻሜ ግጥሚያ ተጨማሪ ማነቃቂያ የሚያስፈልገን አይመስለኝም። በምናውቀው በራሳችን እስታዲዮም ነው የምንጫወተው። ከራሳችን ደጋፊዎችና ህዝብ ጋር ነን። ይህ ራሱ በእጅጉ ያደፋፍረናል። እጅግ በጣም ጥሩ ጨዋታ እንደምናሳይ እርግጠኛ ነኝ። ከ 90 ደቂቃ ጨዋታ በኋላ፣ የሻምፒዮናው ዋንጫ የኛ ሆኖ በሙዑንሸን እንደሚቀር ተስፋ አለኝ።»
ተስፋውን እውን ማድረግ ይቻል ዘንድ፣ ከክለቡ ፕሬዚዳንት ዑሊ ሆነስና አሠልጣኝ ዩፕ ሃይንከስ በትጋት ሲሠሩ ነው የሰነበቱት። እያንዳንዱ ተጫዋች የሚጠበቅበትን ለማሟላት ታጥቆ ተነስቷል። ግብ አዳኝ ማሪዮ ጎሜትዝ ቀኑ መች ደርሶ! እያለ ነው። ዴቪድ አላባ፤ ሆልገር ባድእሽቱበርና ልዊዝ ጉስታቮ ስለተቀጡ እንደማይሰልፉ የታወቀ ነው። ስለሆነም አሠልጣኝ ዩፕ ሃይንከስ ተከላከዩን ክፍል በአዲስ መልክ ማደራጀት ይኖርበታል። ምናልባት አናቶሊ ቲሞሽቹክ ፣ ወደውስጠኛው ተከላካይ ክፍል በመጠጋት ድጋፉን ማጠናከሩ አይቀር ይሆናል። ዲዮጎ ኮንቴንቶ፤ በግራ በኩል አላባን ይተካል። ቶኒ ክሮስም በመሃል ሜዳ ተከላካይነት፤ ልዊዝ ጉስታቮን መተካቱ የማይቀር ነው።
የለንደኑ ክለብ F C Chelsea፣ካፒቴኑ ጆን ቴሪ፣ እንዲሁም ብራኒስላቭ ኢቫኖቪች ፤ ራውል ሜረለስ እና ራሚረስ ስለተቀጡበት፤ አሠልጣኝ ዲ ማቴዎ፣ በአዲስ አሰላላፍ ፤ ብርቱ የማደረጃት ተግባር ነው የሚጠብቃቸው። በመከላከል ረገድ ቆስለው የነበሩት ጌሪ ካሂልና ዴቪድ ልዊዝ አገግመው እንደሚሠለፉ ይጠበቃል። የቡድኑ አምበል የመሃል ሜዳ የአጨዋወት ስልት ቀያሽ ፤ ፍራንክ ላምፓርድ፣ የሙዑንሽኖቹ ሽቫይንሽታይገርና ክሮስ ዘንድሮ ያሳዩት ጨዋታ በዓለም ውስጥ እጅግ ጎበዞች ከሚባሉት የመሃል ሜዳ ተጫዋቾች ተራ የሚያስመድባቸው መሆኑን ጠቅሶ ፤ ዋንጫውን የምግኘቱ ትግል ቀላል እንደማይሆን የ 33 ዓመቱ ጎልማሣ ተጫዋች ገልጿል። ባልደረባው ፣ ታዋቂው ኮከብ ተጫዋች ፤ ዲድዬ(ር) ድሮግባ ም ብርቱ ተጋድሎ ማሳየቱ እንደማይቀር ነው የሚጠበቀው።
ማን ያሸንፍ ይሆን? የሁሉ ጥያቄ ሊሆን ይችላል። የጀርመን ብሔራዊ ቡድን አሠልጣኝ ፤ ዮአኺም ሎኧቭ ፣ «የባየርን ተጫዋቾች በራሳቸው ሜዳ እንደገና ሌላ ሽንፈት እንዲያጋጥማቸው ያደርጋሉ ብዬ ፈጽሞ አሳስብም »ነው ያለው።
አለበለዚያ፤ ለብሔራዊው ቡድን የመለመላቸው 8 የባየርን ሙዑንሸን ተጫዋቾች እንደርሱ አባባል እግር ኳስ እንዳይጠሉ ያሠጋል ። 2000 ጋዜጠኞች የሚከታተሉት የነገው የአውሮፓ የእግር ኳስ ሻምፒዮና የፍጻሜ የዋንጫ ግጥሚያ፤ በዓለም ዙሪያ በ 200 አገሮች በቴሌቭዥን ይታያል።
ተክሌ የኋላ
አርያም ተክሌ