የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባል ጥሪ
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 11 2005
አዲሱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ያገኙትን አድል ተጠቅመው የሃገራቸውን ፖለቲካዊ አካሄድ እንዲያስተካክሉ ተጠየቁ ። ዶቼቬለ ያነጋገራቸው የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባል ጀርመናዊው ግራፍ ላምብስዶርፍ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግልፅ ፖለቲካ ቢያራምዱ የሃገራቸውን እድገት የማፋጠን ትልቅ እድል እንዳላቸው አስታውቀዋል ያነጋገራቸው ሉድገር ሻድሞስኪ ነው ። ዝርዝሩን ሂሩት መለሰ አዘጋጅታዋለች ።
ጀርመናዊው የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባል አሌክሳንደር ግራፍ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በፀረ ሽብር ህግ የታሰሩ ጋዜጠኞችን እንዲለቁ ከትናንት በስተያ በደብዳቤ ከጠየቁት 16 የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባላት አንዱ ናቸው ። ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በአስቸኳይ ና ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ እንዲለቀቅ ጠቅላይ ሚኒስትሩን የጠየቁት ላምብስዶርፍ ና 15 ሌሎች የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባላት በዚሁ ደብዳቤ ኢትዮጵያ ዓለምአቀፋዊውን ሃሳብን በነጻነት የመግለፅ መብትን የማክበር ግዴታ እንዳለበትም አሳስበዋል ። ላምብስዶርፍ ለዶቼቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ እንዳሉት ኢትዮጵያ አሁን የፖለቲካ አካሄዷን ማስተካከል የምትችልበት እድል አላት ።
« ኢትዮጵያ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አዲስ የፖለቲካ ሂደት የመጀመር እድል ያላት ትልቅ ግምት የሚሰጣት ሃገር ናት ። በኛ አመለካከት የኢትዮጵያ መንግሥት ጋዜጠኞችን የሰላ ትችት የሚያቀርቡ ወገኖችን በማህበራዊ መገናና ብዙሃን በትጋት የሚሳተፉ ሰዎችን ፀረ ሽብር በሚባለው ህግ ባይከታተላቸው በጎ ምልክት ይሆን ነበር ። ይህ የፀረ ሽብር የተባለው ህግ የፕሬስ ና ሃብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የሚገድብ ነው ። እንደ አውሮፓውያን እምነት ለአንድ ነፃ አገር ፍጹም መሠረታዊ የሆነ መመሪያ ነው »
አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ከኤርትራ መንግሥት ጋር ለመነጋገር ፈቃደኛ እንደሆኑ በቅርቡ ተናግረዋል ። አቶ ኃይለ ማርያም ለአጀዚሪ በሰጡት ቃለ ምልልስ አስመራም ድረስ ሄደውም ቢሆን ለመደራደር ዝግጁነታቸውን አስታውቀዋል ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለመነጋገር ዝግጁ መሆናቸውን ማሳታወቃቸው ለሰላም በር የመክፈት አዝማሚያ የማሳየታቸው ምልክት ተደርጎ ሊወስድ ይችል ይሆን ተብለው የተጠየቁት ላምብስዶርፍ ሃሳቡ ጠቃሚ ምልክት ነው ብለዋል ።
« በግልፅ እውነት ለመናገር ማንም በትክክል አሁን ያለውን ሁኔታ የሚያውቅ የለም እኔም ብሆን በዚህ ጉዳይ ላይ ቁርጥ ያለ መልስ ለመስጠት እቸገራለሁ ። በግልፅ የሚያታይ ነገር ቢኖር አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አገራቸውን ወደፊት ለማራመድ እድሉ ያላቸው መሆኑ ነው ። ግልፅ ፖለቲካ ቢያራምዱ የህብረተሰቡን በግልፅ የመንቀሳቀስ መብት ቢፈቅዱ ሂስና በነፃ ሃሳብን የመግለፅ መብት እንዲፈቀድ ቢያደርጉ ከጎረቤት አገራት ጋራ ያለው ግንኙነት እንዲሻሻል ቢያደርጉ እዚህ ላይ ወደ አሰመራ ለመጓዝ የቀረበው ሃሳብ ጠቃሚ የሆነ ምልክት ነው ። ይህም ሲሆን በአጠቃላይ እነዚህ ሁሉ ምልክቶች ለኢትዮጵያ እንዲሁም ሃገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ቦታ ትልቅ ግምት የሚያሰጠው ይሆናል ። »
ላምብስዶርፍ በአፍሪቃ ቀንድ የኢትዮጵያ ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው ሆኖም አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ እድሉን ተጠቅመው ሁኔታዎች እንዲንቀሳቀሱ የሚያደርጉ መሆን አለመሆኑ በሂደት እንደሚታይ ተናግረዋል ። ኢትዮጵያ በፀረ ሽብር ህግ የወነጀለቻቸውን ጋዜጠኞች በማሰር ብቻ ሳይሆን በአዲሱ የበጎ አድራጎትና የሲቪክ ማህበራት ህግ ምክንያትም ትችቶች ይቀርቡባታል ። ህጉ ሊያሰራኝ አልቻለም በማለት የጀርመኑ ሃይንሪሽ በል ተቋም በቅርቡ ከኢትዮጵያ ወጥቷል ። ግራፍ ላምብስዶርፍ እንደሚሉት መሰል ተቋማት ተገደው መውጣታቸው ያጎድላል ።
« ኢትዮጵያ የጀርመንንም ሆነ የአውሮፓ ህብረት የልማት ተራድኦውን በተመለከተ ግምት የሚሰጣት ሃገር ናት ። የአዲስ አበባው አስተዳደር ከነዚህ ተባባሪዎቹ ጋር ግልፅና ማስተዋል ያለበት ውይይት የማካሄድ ፅኑ ፍላጎት ማሳየት ሳይኖርበት አይቀርም ። ከዚሁ ጋር የሚያያዘው ከጀርመናውያን እይታ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሥራ መፈቀድ እንጂ መታገድ የለበትም ። ኢትዮጵያ የሚያሳዝነው አንዳንድ አገሮች በሚጓዙበት ፈለግ የምትጓዝ መሆኗ ነው ። ህዝብን ማገዝ የሚሹትን መግታት ሆኗል አካሄዷ ። ሃይንሪሽ በል መሰል ድርጅቶችን ከሃገር ማባረሩ ፤ ራሳቸውን ድርጅቶቹ በቀጥታ አድሎ እንደተፈፀመባቸው ይሰማቸው ይሆናል ። ይህ በቀጥታ የሚታየው ስዕል ነው ። ከበስተጀርባ ግን ለነዚህ የሲቪል ማህበራት ሥራ እንዳያከናውኑ መግታት ነው ። ይህ ደግሞ የህዝቡ ተባባሪዎች ተገደው ሲወጡ የሚያጎድለው ነገር ይኖራል »
ሒሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ