1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአዉሮጳ የገንዘብ ቀዉስና መፍትሔ ፍለጋዉ

ሐሙስ፣ ኅዳር 21 2004

«የአዉሮጳ ሕብረት ቀዉሱን ለማስወገድ መዉሰድ ያለበትን እርምጃ ለማጠናቀቅ የቀሩን አስር ቀናት ወሳኝ ቀናት ናቸዉ።እና በተለይ በሁለት ግንባሮች

https://p.dw.com/p/Rzd7
ምስል picture alliance/dpa

የዩሮ ተጠቃሚ ሐገራት የገጠማቸዉንና የሚያገጥማቸዉን ኪሳራ ለመከላከል የአዉሮጳ ሕብረት የሚያደርገዉ ጥረት አሁንም እንቀደቀጠለ ነዉ።የሕብረቱ በተለይ ደግሞ የዩሮ ተጠቃሚ ሐገራት ቀዉሱን ለማስወገድ የተለያዩ ርምጃዎችን ቢወስዱም ካሰቡት ለመድረስ አሁንም ከባድ ፈተና እንደሚጠብቃቸዉ እየተናገሩ ነዉ።ትናንት ብራስልስ ተሰብስበዉ የነበሩት የሕብረቱ አባል ሐገራት የገንዘብ ሚንስትሮች እንዳስታወቁት ደግሞ ትግሉ ከጊዜ ጋር ጭምር ነዉ።የዶቸ ቬለዉ ክሪስቶፍ ሐሰልባሕ የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ እንደሚከተለዉ አጠናቅሮታል።


ለመሰብሰብ-መወሰን ባለፈዉ ሰኞ የዩሮ ተጠቃሚ ሐገራት የገንዘብ ሚንስትሮች ተራ ነበር።ትናንት ደግሞ የሃያ-ሰባቱም የአዉሮጳ ሕብረት የገንዘብ ሚኒንስትሮች።የሕብረቱ የገንዘብ ኮሚሽነር ኦሊ ሬሕን እንዳሉት ቀዉሱን ለማስወገድ የሚወስደዉ እርምጃ ወሳኝ ደረጃ ላይ ደርሷል።

«የአዉሮጳ ሕብረት ቀዉሱን ለማስወገድ መዉሰድ ያለበትን እርምጃ ለማጠናቀቅ የቀሩን አስር ቀናት ወሳኝ ቀናት ናቸዉ።እና በተለይ በሁለት ግንባሮች፥ማለትም ባንድ በኩል-የገበያዉን መሳከር ለመከላከል አስተማማኝ የገንዘብ ኪሳራ መከላከያን ግንብን በመገንባት ረገድ፥ በሌላ በኩል ደግሞ የምጣኔ ሐብት አስተዳደርን ይበልጥ ማጠናከር»

አንዳዴ የእሳት-ግንብ የሚሉት የአዉሮጳ የገንዘብ ማረጋጋቢ ተቋም ወይም ሥርዓትን ነዉ።EFSF-በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ።ለከሰሩና ለሚከስሩ የዩሮ ተጠቃሚ ሐገራት ገንዘብ የሚያበድረዉ ተቋም የሚኖረዉ የገንዘብ መጠን ከፍ እንዲል ባለፈዉ ሰኞ የተሰበሰቡት የዩሮ ተጠቃሚ ሐገራት የገንዘብ ሚንስርቶች ተስማምተዋል።ምን ያሕል የሚለዉ ግን ግልፅ አይደለም።

እርግጥ ነዉ ተቋሙ አንድ ትሪሊዮን ዩሮ ይኑረዉ የሚለዉ መነሻ ሐሳብ ብዙዎችን ያግባባ ይመስላል።ባለሙያዎች ግን ይሕ ገንዘብ ችግሩን ለማስወገድ መብቃቱን ይጠራጠራሉ።እንደዚያም ሆኖ ለተቋሙ አንድ ትሪሊዮኑን ዩሮ ራሱን የማፅደቁ ሒደት ከየሐገራቱ ሕገ-መንግሥታዊ ድንጋጌዎች ጋር እስኪጣጣም ድረስ መጠበቅ ግድ ነዉ።

Deutschland Haushalt 2012 Haushaltsdebatte Berlin Schäuble
የጀርመን ገንዘብ ሚንስትርምስል dapd

በገንዘብ ቀዉሱ ንረትም ሆነ በሌላ ምክንያት ለኪሳራ የተጋለጡ ኢጣሊያና ስጳኝ የመንግሥት ለዉጥ ማድረጋቸዉ ግን የሲዊድኑ የገንዘብ ሚንስትር አንድረስ ቦርግ እንደሚያምኑት ችግሩን ለማስወገድ ለሚደረገዉ ጥረት ስምረት ጥሩ ድጋፍ ነዉ።

«ሁለት አዳዲስ መንግሥታት በመመሥረታቸዉ መልካም እድል አለን።እነዚሕ መንግሥታት የችግሮቹን አንጓዎች መለየት ይችላሉ።እና ገበያዉ የሚያወላዳ እንዳልሆነ ሊገዘቡትም ይገባል።ይሕን ካደረጉ ታሕሳስ መጀመሪያ ላይ የሚደረገዉ የመሪዎች ጉባኤ በጣም የተሻለ እልባት ለመስጠት ይችላል።ምክንያቱም በገበያዉ የተሻለ ተዓማኒነት ልናይም ስለምንችል።»

ብዙዎች ግን የማሻሻያ ለዉጥ ለማድረግ የሚደረገዉ ዉሳኔ ገበያዉን ያረጋጋል ብለዉ አያምኑም። በርካታ የዩሮ ተጠቃሚ ሐገራት ከአለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት አይ ኤም ኤፍ ብድር እየጠቁ ነዉ።ብድሩ ከአዉሮጶቹ የማረጋጊያ ተቋም ጋር የተቀናጀ መሆን አለበት።በዚሕ መሐል የአዉሮጳ፥ የዩናይትድ ስቴትስ፥ የካናዳ፥ የጃፓን፥ የብሪታንያ፥ እና የሲዊስ ባንኮች የገንዘብ ገበያዉን በጋራ ለመርዳት ትናንት ተስማምተዋል።ስምምነቱ የአክሲዮን ገበያን እንዲያንሰራራ አድርጎታል።

የገበያዉ ማንሰራራት ጥሩ ተስፋ ነዉ።ተስፋዉ ዳር የሚዘልቀዉ ግን የከሰሩት ሐገራት በሁለት እግራቸዉ መቆም ሲችሉ ነዉ።ሐገራቱን ለመርዳት ከሚሰጠዉ ብድር፥ ርዳታ ጎን የባንኮቻቸዉን ወይም የመንግሥታቱን የግምጃ ቤት ሰነድ፥ ወይም ዕዳን መግዛት እንደ ጥሩ መፍትሔ የሚያዩት አልጠፉም።ለከሰሩት የዩሮ ሐገራት ከፍተኛዉ ድጋፍ የምትሰጠዉ ጀርመን ግን የሐገሪቱ ገንዘብ ሚንስትር ቮልፍጋንግ ሼዉብለ ትናንት እንዳሉት ሰነድ-እዳ መግዛቱ ዘላቂ መፍትሔ ይሆናል ብላ አታምንም።

«ከዚሕ (ሽያጭ-ግዢዉ) ጀርባ ያለዉ ምጣኔ ሐብታዊ ትርጉም ችግሩ ይወገዳል የሚለዉን ተስፋ የሚቀንስ ነዉ።ሥለዚሕ ምንም እንኳን የጀርመን መንግሥት በጉዳዩ ላይ ጠንካራ አቋም ባይዝም፥ እንዲሕ አይነቱ እርምጃ ጊዚያዊ ፋታ ከመስጠት ያለፈ የምጣኔ ሐብቱን ችግር ለማስወገድ ብዙም አይጠቅምም ብዬ ነዉ የማምነዉ።ሐሳቡን ሌሎችም ስለሚጋሩት ብቻችን አይደለንም።»

በበርሊን የሚደረገዉ ግፊት አይሏል።ግፊቱ ደግሞ አዉሮጳ ብቻ አይደለም ከዉጪም ጭምር-እንጂ።
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ