1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአሸባሪዎች ጥቃት ሥጋትና ጥንቃቄዉ በጀርመን

ሐሙስ፣ ኅዳር 9 2003

የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትሩ ከሁለት ሳምንት በፊት አጠቃላይ የአሸባሪዎች ጥቃት ሥጋት መኖሩን አስታዉቀዉ ሕዝቡ አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችንና ሰዎችን ለፖሊስ እንዲጠቁም መክረዉ ነበር።ያሁኑ ማስጠንቀቂያቸዉ ግን ካለፈዉ ጠንካራና በተጨባጭ መረጃ ላይ የተመሠረተ ነዉ።

https://p.dw.com/p/QCrX
ደ ሚዚየርምስል picture-alliance/dpa

አሽባሪዎች ጀርመን ዉስጥ አደጋ ለመጠል ማቀዳቸዉን የሚጠቁም መረጃ ማገኘቱን የጀርመን ፌደራላዊ የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስቴር አስታወቀ።የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ቶማስ ደ ሚዚየር ትናንት ማምሻ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳሉት እስላማዊ አሸባሪዎች በያዝነዉ የጎርጎሮሳዉያን ሕዳር ማብቂያ አደጋ ለመጣል ማቀዳቸዉ ተደርሶበታል።ከትናንት ጀምሮ በመላዉ ጀርመን በሚገኙ አዉሮፕላን ማረፊያዎችና ባቡር ጣቢያዎች የሠፈረዉ የፖሊስ ሠራዊት ቁጥርም ጨምሯል።ጀርመንን ከሌሎች ሐገራት ጋር በሚያዋስነዉም ድንበር አካባቢም ቁጥጥር እየተደረገ ነዉ።

«ክቡራትና ክብራን፥ ጥንቃቄ ለማድረግ ምክንያት አለ።የሚያስጨንቅ ነገር-ግን የለም።»

ጀርመን የሽብር አደጋ እንደሚያሰጋት የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ቶማስ ደ ሚዚየር ይሕን በመሰለ አረፍተ-ነገር ሲገልፁ የትናንቱ የመጀመሪያቸዉ ነዉ።በያዝነዉ የጎሮጎሮሳዉያኑ ሕዳር ወር ማብቂያ አደጋዉ እንደሚጣል የሚጠቁመዉ መረጃ የተገኘዉ ደግሞ ከዉጪ ሐገር ነዉ።ከዉጪዉ የተገኘዉ መረጃ እዚሕ ሐገር ዉስጥ ከተጠናቀረዉ አጠቃላይ መረጃ ጋር ተመሳሳይና መረጃዉን የሚያጠናክር- ነዉ።
«(የመረጃዉ) አብዛኛ ጊዜ እና ይዘት በቅርቡ ከተሰባሰበዉ አጠቃላይ መረጃ ጋር የሚመጣጣም በመሆኑ እስካሁን ያለዉን አጠቃላይ መመሪያ (አሰራር) የሚቀይር ነዉ።»

Symbolbild Sicherheitsmaßnahmen nach Terrorwarnung
ጥንቃቄዉ-ባቡር ጣቢያምስል picture alliance/ZB

አደጋዉን ለመከላከልና ተጠርጣሪዎችንም ለመከታተል ለፀጥታ አስከባሪዎች ግልፅና ዝርዝር መመሪያ ተስጧል።የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትሩ አክለዉ እንዳሉት የፌደራል ፖሊስ በተለይ የአዉሮፕላንና የባቡር ጣቢያዎችን በጥብቅ እንዲቆጣጠር ታዟል።

«የፌደራል ፖሊስ ይሕን አደገኛ ሁኔታ ለመከላከል ከሥጋቱ ጋር የሚመጣጠን እርምጃ እንዲወስድ በተለይም በአዉሮፕላንና በባቡር ጣቢያዎች ቁጥጥር እንዲያደርግ መመሪያ ሰጥቻለሁ።ተለወጭ መመሪያ እስኪሰጥ ድረስ ይኸ ገቢር ይሆናል።»

የክፍለ-ሐገራት ፖሊሶች ደግሞ ለጥቃት ኢላማ ይሆናሉ ተብለዉ የሚታወቁ ተቋማትን ይጠብቃሉ።በዚሕም ምክንያት ከወትሮዉ የተለየ የፖሊስ ሠራዊት ቁጥርና እንቅስቃሴ እንደሞኖር ደ ሚዘየር አስታዉቀዋል።
«ዜጎች በርካታ የፖሊስ ሠራዊት ባልደረቦችንና የፖሊስ እንቅስቃሴ ሊያዩ ይችላሉ።ለወትሮዉ ሊታዩ የማይችሉ ብዙ (የጥንቃቄ) እርምጃዎችም ይወሰዳሉ»
የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትሩ ከሁለት ሳምንት በፊት አጠቃላይ የአሸባሪዎች ጥቃት ሥጋት መኖሩን አስታዉቀዉ ሕዝቡ አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችንና ሰዎችን ለፖሊስ እንዲጠቁም መክረዉ ነበር።ያሁኑ ማስጠንቀቂያቸዉ ግን ካለፈዉ ጠንካራና በተጨባጭ መረጃ ላይ የተመሠረተ ነዉ።

«መረጃዎቹ ተጨባች ናቸዉ።ግን የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴና ኑሯችንን ሙሉ በሙሉ የሚቀይሩ አይደሉም።ሊቀይሩ አይገባቸዉምም።ሆኖም ጥንቃቱ ባይፈፀምም እንኳን አንዳድ ጥንቃቄ ማድረግ አለብን።

Terror / Deutschland / Flughafen / Bundespolizei / NO-FLASH
ጥንቃቄዉ-አዉሮፕላን ማረፊያምስል dapd

የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትሩ እንዳሉት ጀርመን ከአጎራባቾችዋና ከሌሎች ወዳጆችዋ ጋር በጥብቅ ትብብር እየሰራች ነዉ።በሚንስትሩ መግጫ መሠረት ከጀርመን ጋር በሚያወሰኑ የጎረቤት ሐገራት ድንበሮችም ቁጥጥር እየተደረገ ነዉ።ይሕ የሚንስትሩ መግለጫ ጀርመንን ለማሸበር ያቀዱት ሐይላት ከዉጪ የሚመጡ ሳይሆኑ አይቀርም የሚለዉን መላምት አጠናቅሮታል።

ፔተር ሽቱትስ

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ