የአስራኤል የጋዛ ድብደባ
ማክሰኞ፣ ኅዳር 11 2005
የእስራኤል የጋዛ ጥቃት ዛሬም ቀጥሎ 6 ፍልስጤማውያን መገደላቸው ተዘግቧል ። ከሟቾቹ መካከል 2 ወጣቶች ይገኙበታል እስራኤል ጋዛን ማጥቃት ከጀመረችበት ካለፈው ሳምንት ረቡዕ አንስቶ የሞቱት ፍልስጤማውያን ቁጥር 116 መድረሱን የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል ። እስራኤል ለሊቱን 100 የሚደርሱ ጋዛ የሚገኙ ዒላማዎችን ከአየር ከባህርና ከምድር መደብደቧንም አስታውቃለች ። ጥቃት ከደረሰባቸው መካከል አንድ ሃማስ የሚገለገለበት ባንክ ይገኝበታል ። የተመድ ዋና ጸሃፊ ፓን ኪሙን እስራኤል በምድር ጦር የጥቃት ዘመቻ ወደ ጋዛ ሰርጥ ሰርጋ እንዳትገባ አስጠነቀቁ። ፓን እንዲህ አይነቱ ድርጊት አደገኛ ሁኔታን የሚቀሰቅስ ነዉ ሲሉ ካይሮ ላይ ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አስታዉቀዋል። በሌላ በኩል ሁለቱም ወገኖች ዉጥረቱን እንዲያረግቡ ፓን ኪሙን በድጋሚ ጠይቀዋል። እንደ አልአራቢያ የዜና ወኪል ዘገባ በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል ሰላም ለማስፈን የተጀመረዉ ድርድር ዉጤት እያሰገኘ ነዉ። የድርድሩ ጥረት የጋዛ ሰርጥን የተቆጣጠረው ሀማስ የሮኬት ድብደባዉን በሚገታበት እና እስራኤል በጋዛ ሰርጥ የጣለችዉን እገዳ በምታላላበት ጉዳይ ላይ ያጤናል። በጋዛ ሰርጥ የተጀመረዉን ውዝግብ ለማስቆም እና ዉጥረቱ ወደ ተባባሰ ችግር እንዳይሻገር ጥረት ለማድረግ የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጊዶ ቬስተርቬለ በኢየሩሳሌም ከእስራኤሉ ፕሪዚደንት ከሺሞን ፔሪስ እና ከጠቅላይ ሚኒስቴር ቤኒያሚን ናትንያሁ ጋር ላይ ተገናኝተዉ፤ ጀርመን ድጋፍ እንደምታደርግ ገልጸዋል። ቬስተር ቬለ እስራኤል ራስዋን የመከላከል መብት እንዳላት በማስታወቅ፤ በአፋጣኝ የተኩስ አቁም ጥረት እንዲደረግም አሳስበዋል።
«ለረጅም ጊዜ በእስራኤል ላይ ሲካሄድ የቆየዉ ውድምቶ የተጠጋውን የሮኬት ጥቃት ትክክለኛ የሚያደርገዉ አንዳችም ምክንያት የለም። የፍልስጤም ባለስልጣናት አቋምም ይህ ነዉ»
የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጊዶ ቬስተር ቬለ ከፍልስጤማውያን ፕሬዚደንት መሃሙድ አባስ ጋር በራማላህ እንደሚገናኙም ይጠበቃል። በሌላ በኩል የዩናይትድ ስቴትስ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሂላሪ ክሊንተን ለሰላሙ ጥረት ወደ እስራኤል እንደሚያቀኑ ተጠቅሶአል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የእሥራኤል የአየር ሃይል በጋዛ ሰርጥ ላይ የጀመረዉን ጥቃት ዛሬም መቀጠሉ ነዉ የተነገረዉ። በጥቃቱ ሁለት ሰዎች መገደላቸዉን ከፍልስጤማውያን ወገን የደረሰዉ ዜና ሲያመለክት፣ የጋዛን ሰርጥን የሚቆጣጠሩት የሀማስ ወታደሮችም ዛሬ ጥዋት ከ30 በላይ ሮኬቶችን ወደ እስራኤል ክልል መተኮሳቸው ተጠቅሶአል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ቱርክን እና የአረብ አገሮች የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮችን ያቀፈ የልዑካን ቡድን ለፍልስጤም ያላቸዉን ድጋፍ ለመግለጽ ጋዛ ሰርጥን ለመጎብኘት መግባታቸዉ ተገልጾዋል። የግብጽ፤ የኩዌት፤ የኢራቅ፤ የቱኒዝ፤ የሞሮኮ እና የሱዳን እንዲሁም የቱርክ ሚኒስትሮች፤ ጋዛ የገቡት፤ በግብጽ በኩል የራፋን ድንበር አቋርጠዉ መሆኑን ከካይሮ የአየር ማረፍያ የደረሰዉን ዘገባ ጠቅሶ የጀርመኑ የዜና አገልግሎት ዘግቦአል።
የግብጹ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሃመድ አማር ለአልጀዚራ ዜና ወኪል እንደገለጹት ፣ ቡድኑ ወደ ሰርጥ የሄደው ለዓረቡ ዓለም ያላቸውን ድጋፍ፣ እንዲሁም፣ ከጋዛ ህዝብ ጎን መቆሙን ለማሳየት ነው። ስለ እስራኤል የጋዛ ድብደባና ውጊያውን ለማስቆም በመደረግ ላይ ስላሉት ጥረቶች የእየሩሳሌሙን ወኪላችንን ዜናነህ መኮንን ስቱድዮ ከመግባቴ በፊት በስልክ አነጋግሬዋለሁ ።
ዜናነህ መኮንን
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ