1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአረፋት አምስተኛ ሙት አመትና ፍልስጤም

ሐሙስ፣ ኅዳር 3 2002

ፍልስጤም-አረፋት፥ ሻሮን ላይመጡ ሔደዋል።ኦል-ሜርት፥ ቡሽ የሉም።ሰላም-ነፃነት ሐገርነትም እንዲሁ።

https://p.dw.com/p/KVFg
የፍፃሜያቸዉ መጀመሪያምስል AP

የፍልስጤም ነፃ አዉጪ ድርጅት (PLO) መሥራችና የረጅም ጊዜ መሪ ያሲር አረፋት የሞቱበት አምስተኛ አመት ትናንት ተዘከረ።አረፋት በሞቱ በሁለተኛዉ ወር የአረፋትን ሥልጣን የያዙት ማሕሙድ አባስ አረፋት የጀመሩትን የፍልስጤሞች የነፃነት ትግልን ዳር ለማድረስ ቃል ገብተዉ ሞክረዉም ነበር።የእስራኤል፥ የአረብ እና የምዕራብ ሐገራት በተለይም የዩናይትድ ስቴትስ መሪዎችም የፍልስጤም እስራኤሎችን ግጭት ዉዝግብ በሰላማዊ በድርድር ለማስወገድ ቃል ያልገቡበት ጊዜ የለም።በተጨባይ ግን ሁሉም የሰላም ችግር በአረፋት ዘመን ከነበረዉ በባሰ ሁኔታ እንቀጠለ ነዉ።ክሌመንስ ፈረንኮተ የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።


ድፍን ፍልስጤም-እንደ ጎበዝ ተማሪ መሐንዲሱን፥ እንደ ወታደር የነፃነት ተዋጊዉ አዋጊዉ፥ እንደ ዲፕሎማት የሰላም ተደራዳሪዉን፥ እንደ ፖለቲከኛ ብልሕ-ብቸኛ መሪዉን ሸኘ በለቅሶ-ሲቃ ሰቆቃ ሸኘ።መአሰላማ-አቡ አምር።ዛሬ አምስት አመቱ።

በሁለተኛ ወሩ ማሕሙድ አባስ-አቡ ማዝን በስልሳ-ከመቶ ድምፅ ለፕሬዝዳትነት ተመረጡ።የአረፋትን ግርማ ሞገስ፥ ጥንካሬ፥ ታማኝ-ተወዳጅነትን ማግኘት በርግጥ የማይታሰብ ነበር።ያም ሆኖ የፍልስጤም እንባ-ለቅሶ ተወዳጅ መሪዉን የመሰናበቺያ እንጂ የእስከ-ዛሬዉ ምናልባትም የወደፊቱም ኑሮ-ሕይወቱ ምራሮት መግለጫ ነዉ-ብለዉ የገመቱ ጥቂቶች ነበሩ።

አባስ ሥልጣኑን እንደያዙ አረፋት አባብለዉ-አለሳልሰዉ ይዘዉት የነበረዉ ሐማስ ለፍልስጤሞች ነፃነት በነፍጥ ከመታገል በስተቀር ሌላ ምርጫ የለም-በሚል አላማዉ ፀና።አባስ ለእስራኤል መሪዎች ተደጋጋሚ ማረጋገጪያ መስጠቻዉ አልቀረም።
«ፀጥታና ደሕንነትን የማስከበሩ ሒደት በሰማላማዊ መንገድ እንደሚከናወን ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ።ግጭቱን ለማስወገድ በወታደራዊ እርምጃ አማራጭ አይደለም።ይሕን ገቢር ለማድረግ እኛ እዉነተኛ ተባባሪዎች ነን።ጠቡን በጋራ ማስወገድ አለብን።»

Mahmoud Abbas West Bank city Ramallah
አባስምስል AP

ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚንስትር ለአርያል ሻሮን ግን አባስ ደካማ መሪ ነበሩ።

አረፋት በሞቱ በስምተኛ ወሩ እስራኤል ጋዛ-ሠርጥን ለቅቃ ወጣች።አባስን ከቁብ ያልቆጠሩት ሻሮን እርምጃዉ የእሳቸዉና የመንግሥታቸዉ ብቻ እንጂ ፍልስጤሞችን የሚመለከት እንዳልሆነ በግልፅ አስታዉቁ።ይሕ የእስራኤል አቋም ለንቋሳዉ አባስ ትንሽም ቢሆን የሚግደረደሩበትን ፖለቲካዊ ትርፍ መና አስቀራቸዉ።አባስ-ሥልጣን የያዙበት አንደኛ አመት ሲከበር በተደረገዉ ምርጫ አክራሪዉ ሐማስ በሙስና የተዘፈቀዉን፥ በጠንካራ መሪ፥ በተባባሪ እጦት ግራ ቀኝ የሚላጋዉን ፈትሕን በቀላሉ አሽንፎ ሥልጣን ያዘ።

የሐማስ ድል ከአባስ-ፋታሕ ይልቅ ለካይሮ-ሪያድ መሪዎች፥ ለእስራኤል፥ ለዩናይትድ ስቴትስና ለአዉሮጳ ሕብረት አስደንጋጭ-አሳሳቢም ነበር።የዩናይትድ ስቴትስና የአዉሮጳ ሕብረት አፃፋ ደግሞ ማዕቀብ።የእስራኤልና የምዕራቦቹ ማዕቀብና ፖለቲካዊ ግፊት ያየለባቸዉ አባስ በሕዝብ የተመረጠዉን የሐማስ መንግሥት አፈረሱት።-ታሕሳስ-ሁለት ሺሕ ስድስት-እንደ አዉሮጳዉያኑ አቆጣጠር።

«አሰቸኳይ ፕሬዝዳንታዊና ምክር ቤታዊ ምርጫ እንዲደረግ ወስኛለሁ።»
የሐማስ መልስ-የታወቀ ነበር።በጋዛ የድርጅቱ ተጠሪ፤-

«አንሳተፍም።ማናቸዉም የምርጫ ሒደት እንዲደረግ አንፈቅድም።አባስ ከደከማቸዉ ሥልጣን መልቀቅ ይችላሉ»

እና የፍልስጤም እስራኤል ግጭት-ዉዝግብ የፍልስጤም-ፍልስጤሞች ሆነ።ጋዛ በፋታሕና በሐማስ ደጋፊዎች ዉጊያ ተደበላለቀች።ሐማስ አሸነፈ።ለአባስ ሌላ-ዉድቀት።የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት ጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ ሥልጣን ሊለቁ አመት ሲቀራቸዉ አናፖሊስ ላይ የጠሩት ጉባኤ ጭል-ጭል የሚለዉን የድርድር ተስፋ ከጥፋት-የሚያድን የማሕሙድ አባስን ፖለቲካዊ ሕልዉና የሚያለመልም መስሎ ነበር።እንደ መሰለ ቀረ።

ባራክ ኦባማ ኦባማ-ባዲስ መንፈስ፥ ካዳዲስ ቃላት-ተስፋ ጋራ ብቅ አሉ።ለፍልስጤሞች ግን ጠብ ያለ ነገር የለም።እስራኤልም በሐይል በያዘቸዉ ግዛት የአይሁድ ሠፈራ መንደሮችን ማስገንባትዋን ቀጠለች።የሐማስ አባል ዶክተር ካሚስ ናጂር-


«የአሜሪካ መርሕ ቋሚ ነዉ።አዲስ ፕሬዝዳት ተመርጧል።የአሜሪካ መርሕ ግን ያዉ የድሮዉ ነዉ።የአዉሮጳ መርሕም ያዉ ራሱ ነዉ።እስራኤልን የመሠረቱት እነሱ ናችዉ።እሳሬን ይደግፋሉ።(ለነሱ) እስራኤል ሁል ጊዜ ልክ ነች።ፍልስጤሞች ደግሞ ጥፋተኞች።»

አባስ የቀራቸዉ አንዲት ጥይት ነበረች።ሥልጣን-መልቀቅ።በጥሩ ምርጫ-ዳግም አል-ወዳደርም አሉ።ፍልስጤም-አረፋት፥ ሻሮን ላይመጡ ሔደዋል።ኦል-ሜርት፥ ቡሽ የሉም።ሰላም-ነፃነት ሐገርነትም እንዲሁ።

ክሌመንስ ፈረንኮተ/ ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ