1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአለም አቀፉ የፍልሰት ፖሊሲ

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 9 1999

ዛሪ ታህሳስ ዘጠኝ በአለም አቀፍ ደረጃ ፍልሰት ቀን ተብሎ ታስቦ ዉሎአል። ይህንኑ ፍልሰት ቀን በማሰብ ባለፈዉ ሳምንት መጨረሻ የአዉሮፓዉ ህብረት የመንግስት ባለስልጣናት እና መሪዎች በብረስልስ ጉባኤ አድርገዉ ነበር

https://p.dw.com/p/E0hb

በጉባኤዓቸዉ ላይ ፍልሰትን በአዉሮፓ ህጋዊ ማድረግ እና በአዉሮፓዉ ህብረት አባል አገራት አንድ ጉዳዩን የሚያዉቅ ማዕከላዊ ቢሮ የመኖር አስፈላጊነት ላይ ተነጋግረዋል። ነገር ግን ይህ አይነቱ ለአመታት የዘለቀ ዉይይት በእዉነት ተግባራዊ ይሆናል የሚለዉ የህብረቱን አባል አገራት ዲፕሎማቶች አጠያያቂ አድርጎአል። የአዉሮፓዉ ህብረት አባል እና የወቅቱ የፍልሰት ፖለቲካን በተመለከተ ከብረስልስ ተዘግቦአል።

የአዉሮፓዉ ህብረት ኮሚሽን እስከ ሚቀጥለዉ የአዉሮፓዉያኑ አመት አጋማሽ ማለት የጀርመን የርዕስነት ዘመኗን በምታጠናቅቅበት ወቅት ህብረቱ ስለ ህገ-ወጥ ስደተኞች እና ፍልሰትን በተመለከተ በተለይም ከህብረቱ አባል አጋራት ዉጭ ካሉት አገራት ጋር ተፈጻሚነት እንዲኖረዉ ያለዉን አቃም እና አመራር ማቅረብ አለበት። ይኸዉም የሚቀርበዉ ፖሊሲ ፈላሾች ወይም ጥገኝነት ጠያቂዎች ከሚመጡበት ወይም ትዉልድ አገራት ጋር የወዳጅነት ግንኙነቱ በተጠናከረ መልክ ታስቦ መቀየስ አለበት ነዉ። በብረስልስ ጉባኤ ላይ የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክል ባሰሙት ንግግር
«ህገወጥ ስደተኞች ከትዉልድ አገራቸዉም ተሻግረዉ ከሚመጡበት አገራት ጋር በወዳጅነት የጋራ የሆነ የትብብር ስራ መፈጸም እንዳለብን ጽኑ እምነት አለን»

ስደተኞችን በተለያየ ቦታዎች ማዘዋዋወር በሚል በጉባኤዉ ላይ የህብረቱ ህግ አማካሪ Franco Frattini ያመጡትን ሃሳብ የአባል አገራቱ ተወካዮች ሃሳቡን የተቀበሉት ይመስላል። እ.አ አቆጣጠር በ60 ዎቹ እና 70 ዎቹ አመታት ጀርመን እንግዳ ሰራኞችን ከተለያየ አገር ማምጣትዋን ምሳሌ አድርገዉ ጠቅሰዉም ነበር። ነገር ግን ይህ አይነቱ ሃሳብ እንደታሰበዉ ተግባራዊ ይሁን አይሁን አጠያያቂ ነዉ, ምክንያቱም እዚህ ላይ እንግዳ ሰራተኞች ሲባል በእንግድነታቸዉ ዘመን ተግባራቸዉን ፈጽመዉ ወደ መጡበት አገር ይመለሳሉ፣ ወይንስ በእንግድነት እዝያዉ ቀልጠዉ ይቀራሉ ነዉ። የአዉሮፓ ህብረት ኮሚሽን እስከ መጭዉ ሰኔ ወር ድረስ በነዚህ ጉዳዮች ላይ ጥናቱን ጨርሶ ለህብረቱ የጥናቱን ዉጤት ማቅረብ አለበት።

እዚህ ላይ ጥያቄዉ ስንት እንግዳ ሰራተኞች ወይም በፍልሰት ለስራ ወደ የትኛዉ የህብረቱ አባል አገሮች ይምጡ ለምን ያህል ግዜስ የሚለዉ ነዉ። የአዉሮፓዉ ህብረት ህገወጥ ስደተኞችን ለመግታት የመጡበትንም አገር ለመቆጣጠር ለምሳሌ በሰሜናዉ አፍሪቃ ጠረፍ በኩል ወደ መሃል አዉሮፓ ለመዝለቅ የሚጥሩትን እዝያዉ አንድ መአከል በመክፈት ስደተኞች ወድየትኛዉ አገር ጥገኝነት እንደሚፈልግ በመጠየቅ መመርመር አለበት የሚል ሌላ ሃሳብም ቀርቦአል።

የህብረቱ ኮሚሽነር Frattini በማበከር እንደገለጹት ከአንድ ወር በፊት በሊቢያ መዲና ትሪፖሊ ስደተኞችን በተመለከተ የተደረገዉ አዉሮፓ አፍሪቃ ጉባኤ ምንም ያህል ፋይዳ አላስገኘም ባይ ናቸዉ
«በመጀመርያ ደረጃ የስደትን ዋና ስር ነቅሎ ለመጣል፣ ዋና ምክንያት የሆነዉን ድህነት እና ስራ አጥነትን መዋጋት ነዉ። ስደተኞች ከሚፈልሱበት አገር ዉስጥ የስራ ቦታን ለመፍጠር እና በኢኮኖሚ እድገትን ለማምጣት አዉሮፓ ከአፍሪቃዉ ህብረት ጋር የትብብር ስራን ትሻለች።

በእንደዚህ አይነት የአዉሮፓዉ ህብረት በብረስልስ ህገወጥ ስደተኞችን እና የሚፈልሱ ህዝቦቹን ለመግታት ሃሳብ ተለዋዉጦአል። በተለይ በሰሜን እና ምዕራብ አፍሪቃ ጠረፍ በኩል ጀልባ በመታገዝ በከፍተኛ መጠን ወደ ጣልያን ደሴት ላምፓዱሳ እና ማልታ ስደተኛ ገብተዋአል። ጥናቱም እንደሚያስረዳዉ የጣልያን እና የስፔን ፖሊስ በዚህ አመት ብቻ 44 ሺህ የጀልባ ስደተኞችን ይዞአል። እዚህ ላይ የሚያሳዝነዉ ደግሞ በጀልባ ወደነዚህ አገሮች ለመግባት ብለዉ የሰመጡት የአፍሪቃዉያን ቁጥር በጣም በርካታ መሆኑ ነዉ። የአዉሮፓዉ ህብረት በያዝነዉ አመት ዉስጥ የድንበር ቁጥጥርን በማጠናከር በተለይ በአትላንቲክ ወቅያኖስ እና ሜዲተራንያን ባህር አቅራብያ ያሉትን ወደቦች ቁጥጥር አተናክሮአል። በፖላንድ መዲና ዋርሶ የሚገኘዉ FRONTEX ተብሎ የሚታወቀዉ ድንበር መቆጣጠርያ ቢሮ በተለይ ሜዲተራንያን ባህር ጥበቃ ተጠናክሮ ይገኛል። በአዉሮፓዉ ህብረት የስደተኞች ጉዳይ አዋቂ አፍሪቃዉያን ስደተኞች በአዉሮፓ በቁጥር በጣም ጥቂት መሆናቸዉን ይገልጻሉ። በአንጻሩ ይላሉ ወደ በአዉሮፓዉ ህብረት አገሮች ያለምንም ችግር በምስራቅ አዉሮፓ በኩል ተሻግረዉ የገቡ ከ300 እስከ 600 ሺህ የሚገመቱ ህገወጥ ስደተኞች እንደሚኖሩ ተነግሮአል።