የንጹሕ ዉኃ አቅርቦት ጥያቄ
ማክሰኞ፣ መጋቢት 13 2008የዓለም የጤና ድርጅት ንጹሕ ዉኃ ማግኘት ማለት ከዉኃ ወለድ በሽታዎች ስጋት መዳን ነዉ ይላል። ዉኃ ዓለማችን ከተሸከመቻቸዉ የተፈጥሮ ሃብቶች የሚበረክተዉ ቢሆንም የአያያዝ ጉድለቱ እንዳለ ሆኖ ያለዉም ንጹሕ ዉኃ ለሁሉም መዳረስ አለመቻሉ ዛሬም መነጋገሪያ እንዲሆን አድርጎታል።
በዩኒሴፍ ኢትዮጵያ የዉኃ አቅርቦትና የንጽሕና አጠባበቅ መርሃግብር ኃላፊ ዶክተር ሳሙኤል ጎድፍሬ ኢትዮጵያ የንጹሕ ዉኃ አቅርቦት በሚያሳየዉ መሻሻል አበረታች መሆኑን ይናገራሉ።
ምንም እንኳን በአምዓቱ የልማት እቅድ መሠረት ንጽሕናዉ የተጠበቀ የመጠጥ ዉኃ ለማዳረስ ጥረት ቢደረግም አሁንም ቢሆን አብዛኛዉ ሕዝብ ዉኃ ለማግኘት ረዥም መንገድ በመጓዝ የወንዝ እና የምንጭ ዉኃን እንደሚጠቀምም ዶክተር ጎድፍሬ ያስረዳሉ።
እንዲህ ያለዉን የዉኃ እጥረት እና የንጹሕ ዉኃ አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ ዩኒሴፍ ሌሎችም እንዲሳተፉበት በመጋበዝ የጀመረዉ እንቅስቃሴ መኖሩን በጽሁፍ ባሰራጨዉ ጋዜጣዊ መግለጫ ጠቅሷል። ዩኒሴፍ ከአጋሮቹ ጋር በመተባበር ፕሮጀክት ቀርጾ፤ እስከመጪዉ አራት ዓመት ድረስ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ንጹሕ ዉኃ እንዲያገኝ ለማድረግ እየሠራ እንደሆነ ይገልጻል።
የአየር ንብረት ለዉጥ የዝናብ መታጣትን ብቻ አይደለም የሚያስከትለዉ። ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ እና የተዛባ አመጣጥም ሌላዉ መገለጫዉ ነዉ። ሲያሻዉ ደግሞ ከሚገመተዉ በላይ ሊዘንብ ይችላል።
ዩኒሴፍ በመላዉ ዓለም ንጹሕ ዉኃ ለሁሉም እንዳይዳረስ እንቅፋት ከሆኑት ነገሮች አንዱ የጽዳት አጠባበቅ ጉድለት መሆኑን ያመለክታል። 2,4 ቢሊየን ሰዎች በመላዉ ዓለም ተገቢዉ የመጸዳጃ ቤት የመጠቀም እድሉም ሆነ አቅሙ የላቸዉም። በባህር ላይ እንደተገኘ የሚጣለዉ ቆሻሻና በካይ ኬሚካልም ሌላዉ የችግሩ መንስኤ መሆኑን ስለዉኃ ምንጮች ንጽሕና መጠበቅ የሚሟገቱ ወገኖች ደጋግመዉ ያሳስባሉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ