1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የናይጀር ደለል ይዞታ

ቅዳሜ፣ ግንቦት 27 2008

የናይጀሪያ መንግሥት በኒዠር ደለል በሚገኘው የኦጎኒ ግዛት በነዳጅ ዘይት ፍሳሽ የተከሰተውን ያካባቢ ብክለት ለማስወገድ ያስችላል ያለውን ግዙፍ የማፅዳት ፕሮዤ ጀመረ። ርምጃውን ለተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃ የሚሟገቱት በደስታ ተቀብለውታል።

https://p.dw.com/p/1J0Fu
Nigeria Militär-Patrouillen im Niger-Delta
ምስል DW/M. Bello

የናይጀር ደለል ይዞታ

« መርሀ ግብሩ መነቃቃቱ ለኛ የአካባቢ ተቆርቋሪዎች ጥሩ ጅምር ነው። ምክንያቱም፣ አንደኛ፣ ከመርሀ-ግብሩ በስተጀርባ ፕሬዚደንታዊው ጽሕፈት ቤት እና ፌዴራዊው መንግሥት ስላሉበት ቀጣይነቱ የተረጋጋገጠ ነው። ሁለተኛ ደግሞ፣ ከብዙ ጊዜ ወዲህ አካባቢ ጥበቃን በተመለከተ ፍትሕ ተነፍጓቸው ለቆዩት የኦጎኒ ላንድ ነዋሪዎች በመጨረሻ ፍትሕ የሚያስገኝላቸው ነው።»


ይኸው አንድ ቢልዮን ዶላር የሚጠይቀው መርሀ-ግብር፣ በተመድ ግምት መሰረት፣ እስከ 30 ዓመታት ድረስ ሊወስድ ይችላል። ይህንኑ ከአምስት ዓመት መዘግየት በኋላ የተነቃቃውን ፕሮዤ የናይጀሪያ ፕሬዚደንት መሀመዱ ቡሀሪ መርቀው እንዲከፍቱት ታቅዶ ነበር። ይሁንና፣ ፕሬዚደንቱ በአካባቢው በሚታየው የፀጥታ ስጋት ምክንያት ይህንኑ ዕቅዳቸውን በመሰረዝ በምክትላቸው የሚ ኦሲንባዦ ተወክለዋል።

Nigeria Abuja Präsident Muhammadu Buhari
ምስል picture-alliance/dpa/M. van Dijl

ላለፉት ሰባት ዓመታት መረጋጋት ታይቶበት በነበረው በዚሁ አካባቢ አሁን እንደገና በዚሁ አካባቢ ነዳጅ ዘይት እና ጋዝ በማውጣቱ ስራ የተሰማሩ የውጭ ተቋማትን ዒላማ ያደረጉ የሚታገል ራሱን የ«ናይጀር ዴልታ አቬንጀርስ» ብሎ የሚጠራ ቡድን ፕሬዚደንት ቡሀሪ መርሀግብሩን ለመመረቅ ወዳካባቢው ከሄዱ እንደሚገድላቸው ዛቻ እንዳሰማ ነው የሀገሪቱ መንግሥት ያስታወቀው። ቡድኑ ከአካባቢው የሚመረተው ነዳጅ ዘይት እና ጋዝ የሚገኘው ገቢ ተጠቃሚ ለመሆን፣ ብሎም፣ ለአካባቢው ጥበቃ እና ልማት ድርሻ እንዲያበረክት የሚታገለው ቡድን ሚሊሺያዎች ካለፉት ጥቂት ሳምንታት ወዲህ በዚሁ በነዳጅ ዘይት እና ጋዝ በታደለው ግዛት የነዳጅ እና የጋዝ ማስተላለፊያ ቧንቧዎችን በተደጋጋሚ በማፈንዳት ጥቃታቸውን አጠናክረዋል። እና ቡሀሪ ወዳካባቢው አለመሄዳቸው፣ ኡኮቹ ኩቺሜዜን የመሳሰሉ የናይጀሪያ ዜጎች እንደሚሉት፣ የግድያውን ዛቻ እንደዋዛ አለማየታቸውን ጠቁሞዋል።

« እርግጥ ነው፣ የፀጥታው ጉዳይ አሳሳቢ ሆኖ አግንተውታል። ምክንያቱም፣ እነዚህ ራሳቸውን «ናይጀር ዴልታ አቬንጀርስ» ብለው የሚጠሩት ቡድን ሚሊሺያዎች መንቀሳቀስ ከጀመሩ ወዲህ ያሰሙትን ዛቻ ተግባራዊ ያላደረጉበት አንድም ጊዜ የለም። ከጥቂት ጊዜ በፊት የጥቃታቸው ዒላማ የ«ሼብሮን» ተቋም ነበር። እና ፕሬዚደንቱ በፀጥታ ምክንያት መሰረዛቸው አያስገርምም። » ፕሬዚደንቱ ወደ ኦጎኒላንድ በመሄድ መንግሥታቸው ለዚያ አካባቢ ሕዝብ ደህንነት እና ልማት እንደሚሰራ ሊያሳዩ ይገባ እንደነበረ የማህበራዊ ጉዳዮች ተንታኝ ዋሌ ፋታዴ ነው ያስረዱት።

Nigeria Niger-Delta Ölverschmutzung Kläger Eric Dooh
ምስል picture-alliance/dpa/M. van Dijl


« ፕሬዚደንቱ ወደዚሁ አካባቢ በመሄድ እንደ አንድ ናይጀሪያዊ ለሕዝቡ መቆማቸውን ማሳየት የሚያስችላቸውን አጋጣሚ ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል ብየ አስባለሁ። አለሁላችሁ ማለት በቻሉ ነበር። ግን አላደረጉትም። በምረቃው ሥነ- ስርዓት እንዲገኙ መጨረሻ ደቂቃ ላይ ምክታላቸውን መላካቸው መጥፎ ነው። »


«ሮያል ዳች ሼል ን እና «ሼቭሮን»ን የመሳሰሉ የውጭ ተቋማት የሚሰሩበት የናይጀር ደለል ነዋሪዎች ከተቋማቱ የሚለቀቀው ፍሳሽ አካባቢያቸውን በመበከል በጤና ላይ እክል እያደረሱ ነው በሚል እና የናይጀሪያ መንግሥትም ከነዳጅ ዘይቱና ጋዝ ሽያጭ ከሚያገኘው ገቢ አካባቢውን ተጠቃሚ አላደረገም ሲሉ ለብዙ ዓመታት ቅሬታቸውን ማሰማታቸው የሚታወቅ ሲሆን፣ ለአካባቢው ሰፊ ራስ ገዝ አስተዳደር ይሰጥ በሚል አንዳንዶች የብረት ትግል መጀመራቸው ይታወቃል።
የ«ናይጀር ዴልታ አቬንጀርስ » ሚሊሺያዎች በኦጎኒላንድ ጥቃታቸውን የቀጠሉበት ርምጃቸው በነዳጅ ዘይቱ ምርት ላይ ጥገኛ የሆነውን የሀገሪቱን ምጣኔ ሀብት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን በሌጎስ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር ሲልቬስተር ኦዲዮን አኬይን አስታውቀዋል።


የ«ናይጀር ዴልታ አቬንጀርስ» ባጭር ጊዜ ውስጥ ሀገሪቱ በንግድ በየቀኑ ወደ ውጭ የምትልከውን 2,2 ሚልዮን በርሜል ነዳጅ ዘይትን ወደ 1,4 ሚልዮን በርሜል እንዲቀንስ አድርጎዋል። » ሲልቬስተር ኦዲዮን አኬይን አክለው እንዳስረዱት፣ የ«ናይጀር ዴልታ አቬንጀርስ» በጀመረው ጥቃት ናይጀሪያን ምጣኔ ሀብት ብቻ ሳይሆን ተቀባይ ሀገራትንም ዒላማ አድርጓል።

Nigeria Niger Delta Ölverschmutzung Kind Öl
ምስል picture-alliance/dpa/W. Krumm


« የ«ናይጀር ዴልታ አቬንጀርስ» ትግል አካባቢዋቸው እና ነዋሪው ለብዙ ዓመት ደርሶበታል በሚለው ድርጊት አንፃር ያተኮረነው። ምክንያታቸው ተዓማኒ ነው አይደለም ሌላ ጥያቄ ነው። በዚያም ሆነ በዚህ ግን ናይጀሪያን ከዓለም አቀፉ ኤኮኖሚ ጋር የሚያገናኘው የነዳጅ ዘይቱ እንዱስትሪ እየተዘጋ ነው።
የናይጀሪያ መንግሥት ደግሞ ለዚሁ ችግር መፍትሔ ያገኘለት አይመስልም። »

አርያም ተክሌ

አዜብ ታደሰ