የታገደው የበቆሎ ንግድ ስምምነት
ማክሰኞ፣ መጋቢት 5 2009ባለፈዉ ሳምንት የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ም/ቤትና የምሥራቅ አፍሪቃ የእህል ም/ቤት ፣በኢትዮጵያ የእህል ነጋዴዎች እና በምሥራቅና በደቡብ አፍርቃ ሸማቾች መካከል የሚደረግ የእህል ሽያጭን የሚያመቻች የጋራ ዉይይት በአድስ አበባ አዘጋጅተው ነበር። 55 ሚልዮን ዶላር የሚያወጣ ወደ 275,000 ሜትርክ ቶን ቦቆሎና ጥራጥሬ ከኢትዮጵያ ወደ ምስራቅና ደቡብ አፍርቃ ለመሽጥ 51 ዉሎች መፈረማቸውን የምሥራቅ አፍሪቃ የእህል ምክር ቤት ያወጣው መግለጫ ያትታል። በኢትዮጵያ 10.2 ሚልዮን ሰዎችን ያጠቃዉ ድርቅ በአገሪቱ የእህል ምርት እንዲቀንስ ማድረጉ ሲዘገብ ቆይቶዋል። ይህን የእህል እጥረት ለመቋቋምም የኢትዮጵያ መንግስት የበቆሎንና ማሽላ ምርት ለውጭ ገበያ እንዳይውል እገዳ ጥሎ እንደነበርም ይታወሳል።
ይህ እገዳ በምን ደረጃ ላይ ይገኛል ብዬ በንግድ ሚኒስቴር የህዝብ ግኑኝነት የኮሙኒኬሼን አስተባባር የሆኑት አቶ ሽመልስ አረጋን ጠይቄ ነበር። ቦቆሎም ይሁን ማሽላ ወደ ዉጭ አገር ለመላክ መጀመርያ ምርቱ የአገር ውስጥ ፍጆታ የሚሸፈን መሆን አለበት ፤ ከዚህ ሌላ የድርቅ ሁኔታዎች ከተሻሻሉ በኋላም እገዳው ሊነሳ ይችላል የሚሉት አቶ ሽመልስ እገዳዉ በዚህ ጊዜ ይነሳል ብሎ መናገር እንደምከባቸዉ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። በተደረገዉ ዉይይት ላይ ንግድ ምንስቴር አለታገበዝም፣ «የኛ ሰዎችም አልተሳተፉም» ይላሉ አቶ ሽመልስ። ስለዚህ ዉሉን መፈራራማቸው እገዳዉን መጣስ ነዉ የሚሉት አቶ ሽመልስ መንግስት ሊወስድ የሚችለዉን ርምጃ ተናግራረዋል።
የአድስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ም/ቤት በጉዳዩ ላይ ማብራርያ እንድሰጠን ጠይቀን ነበር። ኢትዮጵያ ከምስራቅ አፍሪቃ ዋነኛ የበቆሎ አምራች እንደሆነችና ከአፍርቃ ዉጭ ወደ አዉሮጳና ወደ አሜርካም ምርቱን እንደምትልክ የም/ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ኤልያስ ገነቲ ይናገራሉ።
ስለ እህል ሽያጭ ውሎቹ ጋዜጣዊ መግለጫዉን ያዘገጀውን የምሥራቅ አፍሪቃ የእህል ም/ቤት በስልክም በኢሜሊም ማብራርያ ኢንዲሰጠን በተደጋጋሚ ሙከራ ብናደርግም መልሳቸዉን ልናገኝ አለቻለንም።
መርጋ ዮናስ
ኂሩት መለሰ