የቭየናው የሶሪያ የሰላም ንግግር
ዓርብ፣ ጥቅምት 19 2008
ሶሪያ ባልተሳተፈችበት በዚሁ ንግግር ላይ ከተካፈሉት መካከል የዩናይትድ ስቴትስ ፣ የብሪታንያ፤ የጀርመን የፈረንሳይ የሩስያ እንዲሁም የኢራን እና የሳውዲ አረቢያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ና የቻይና ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይገኙበታል ። ዛሬ ዓለም ዓቀፍ ንግግር ተጀመረ።በንግግሩ ላይየ 17 ሃገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች፤ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እና የአውሮፓ ህብረት ተወካዮች ተካፍለዋል።ሶሪያ ባልተሳተፈችበት በዚሁ ንግግር ላይ ከተካፈሉት መካከል የዩናይትድ ስቴትስ ፣ የብሪታንያ፤ የጀርመን የፈረንሳይ የሩስያ እንዲሁም የኢራን እና የሳውዲ አረቢያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ና የቻይና ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይገኙበታል ። የሶሪያው ፕሬዝዳንት በሽር አል አሳድ የረዥም ጊዜ ደጋፊ ኢራን በዚህን መሰሉ ንግግር ስትካፈል የመጀመሪያዋ ነው ። የሃገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሀመድ ጃቫድ ዛሪፍ ከስብሰባው በፊት በሰጡት አስተያየት በሶሪያ ሰላም ለማውረድ አራት ደረጃዎችን መከተል ይገባል ብለዋል ።
«የሶሪያ የሰላም እቅድ የሚከተሉት ደረጃዎች ሊኖሩት ይገባል ።ግጭቱን ማስቆም ፣ሽብርን በጋራ መዋጋት ፣ብሔራዊ የአንድነት መንግሥት መመስረት ፣ እና በሶሪያ ህዝቦችና በሶሪያ ቡድኖች መካከል ውይይት በማካሄድ መፍትሄ ላይ መድረስ »
እስከ ዛሬ ከንግግሩ ተገልላ የነበረችው ኢራን አሁን መካፈሏ ለጦርነቱ መፍትሄ ለመሻት ወሳኝ ሚና ሊኖረው ይችላል የሚል ተስፋ ተጥሎባታል ።የዛሬው ንግግር ትኩረት በሶሪያው ፕሬዝዳንት በበሽር አል አሳድ የወደፊቱ እጣ ፈንታ ላይ ነው ።ዩናይትድ ስቴትስና የአረብ ሃገራት አጋሮችዋ አሳድ እንዲነሱ ይፈልጋሉ ።ኢራን ደግሞ ከ6 ወራት የሽግግር ጊዜ በኋላ በሚካሄድ ምርጫ የበሽር አል አሳድ እጣ ፈንታ ይወሰን በሚለው ሃሳብ ነው የምትስማማው ።ሆኖም የአሳድ ጠላቶች አሳድን ለማንሳት ሌሎች እርምጃዎች ካልተወሰዱ በስተቀር አዲስ ምርጫ የአሳድን የሥልጣን እድሜ ማራዘሚያ ነው የሚሆነው ሲሉ ይቃወማሉ ።የአስተናጋጅዋ የኦስትሪያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሴባስትያን ኩርትስ የዛሬው ንግግር ውጤት እንዲያስገኝ ልዕለ ኃያላኑና በሶሪያ አካባቢ የሚገኙ ኃያል ሃገራት በሶሪያ ጉዳይ ላይ አንድ አግባቢ ሃሳብ ላይ መድረስ እንደሚገባቸው አሳስበዋል ።« ልዕለ ኃያላኑ ዩናይትድ ስቴትስና ሩስያ ብቻ ሳይሆኑ በአካባቢውም ያሉ ኃያል ሃገራት በሃሳብ መቀራረብ ይኖርባቸዋል ። የአካባቢው ኃያላንና ልዕለ ኃያላኑ ሂደቱን በጋራ ለመደገፍ አንድ አቋም ሲይዙ ብቻ ነው አጠቃላይ ሂደቱ ስኬታማ ሊሆን የሚችለው »
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሀመድ