የብሬመርሃፈን የፍልሰት መታሰቢያ ቤተ መዘክር
ማክሰኞ፣ ግንቦት 27 2005በሰሜን ምዕራብ ጀርመኑ የብሬመን ፌደራዊ ክፍለ ግዛት ሥር የምትገኘው የወደብ ከተማ ብሬመርሃፈን የንግድ ና የኢንዱስትሪ ከተማ ናት ። ከተማይቱ ወደብ እንደመሆኗና በአቀማመጧ አመቺነትም የንግድ ብቻ ሳይሆን የሰዎች እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ ሲካሄድባት ቆይቷል ። ይህ መነሻ ሆኖም የበርካታ ጎብኚዎችን ቀልብ የሚስብ ቤተ መዘክር በከተማይቱ ይገኛል ። የዶቼቬለ የአማርኛ ክፍል ባልደረባ ተክሌ የኋላ ባለፈው ሳምንት ወደ ብሬመን ለሥራ በሄደበት አጋጣሚ ከተቋቋመ የፊታችን ነሐሴ 8 አመት የሚሞላውን ይህን ቤተ መዘክር የማየት እድል አጋጥሞት ነበር ። በቤተ መዘክሩ ያየውንና የሰማውን እንዲሁም ስለ ጀርመኖች ፍልሰት የሚያውቀውን በዚህ ዝግጅት ያካፍለናል ። የብሬመንሃፈን የፍልሰት መታሰቢያ ቤተ መዝከር ምን እንደሚመስል ከቤተ መዘክሩ አመሰራረት በመነሳት በዓይነ ህሊና ያስቃኘናል ። የብሬመርሃፈኑ የፍልሰት ቤተ መዘክር በወደቡ በኩል የሄዱ ስደተኞችን ማንነት የሚገልጹ በዘመን አመጣሹ ቴክኖሎጂ የተደገፉ መረጃዎች ለተጠፋፋ ቤተሰቦች ትልቅ ተስፋ እየሰጡ ነው ። ቤተ መዘክሩን ለመጎብኘት ከሚመጡት ጀርመናውያን መካከል ዘመዶቻቸው ያሉበትን የሚፈልጉ አሉ ። ከነዚህ መካከል ተክሌ ያነጋገራቸው እኚህ አዛውንት ይገኙበታል
« በእኔ ወገን በኩል ከዚህ ፈልሶ የሄደ ዘመድ የለም ። በባልተቤቴ በኩል ግን ድሮ ወደ አሜሪካ የፈለሱ መኖራቸውን ከመዛግብትም በመርመር አግኝተናል ወደ ቤታችንም ሄደን እስቲ እውነት ከሆነ ለማጣራት አሰሳውን በዚህ ረገድ እንቀጥላለን ።»
ሌላዋ ጎብኚም የዘመዶቻቸውን ስም በቤተ መዘክሩ ውስጥ ካለው ሰነድ ማግኘት መቻላቸው አስደስቷቸዋል ።
« ይህን ልብ ሰቃይና በሚያስደንቅ ሁኔታ የተደራጀ ቤተ መዘክር አሁን ከጎበኘሁ በኋላ ትውልድ ሃገርን በሚቆጠቁጥ ሁኔታ ከለቀቁት መካከል ሁለቱን አክስቶቼን( የእናቴን እህቶች) እፈልጋለሁ ። ሌላዋ አክስቴ «ኬድ» ከባለቤቷ ጋር ከጦርነቱ ፍፃሜ በኋላ ተገናኝተን ተዋውቀናል ። ባለቤቴም እህቶቹ ሁሉ ካናዳ ነው የሚኖሩት ። አክስቴና ባሏ ያኔ በ20 ዶላር ክፍያ ነው ፈልሰው ካናዳ የገቡት ። እንግሊዘኛም ከሞላ ጎደል መናገር አይችሉም ነበር ። ሆኖም በዚያ ኑሮአቸውን መስርተዋል ። የአክስቴም ልጆች ሁሉ ካናዳ ነው የሚኖሩት ። የስም ዝርዝራቸውን ከፈላስያኑ ስም ዝርዝር ውስጥ በማግኘቴ በጣም ነው የደነቀኝ ።»ብሬመርሃፈን፣ እጎአእስከ 1890 ድረስብቻቁጥራቸውወደ1.2 ሚሊዮን የሚደርስ ጀርመናውያን ወደ ተለያየየ ዓለም ክፍልየሚያደርጉትጉዞ መነሻ ነበረች። በዚህች ወደብ በኩል ባለፉት 300 አመታት በአጠቃላይ ቁጥራቸው7.2 ሚሊዮን የሚጠጋ ሰዎች ወደተለያዩ አገሮች እንደፈለሱ ይገመታል ። ሰዎቹን ለመሰደድ ካበቋቸው ምክንያቶች ውስጥ ኢኮኖሚያዊ ና ፖለቲካዊ ችግሮች በዋነኝነት ይጠቀሳሉ ።
በልዩ ልዩ ምክንያቶች ወደተለያየ የዓለም ክፍል ከተሰደዱት በርካታ ጀርመናውያን መካከል በሄዱበት አገር ለከፍተኛ ክብርና ዝና የበቁ በተሰደዱበት ሃገርም ብዙ አስተዋፅኦ ያበረከቱ ጀርመናውያን ይገኙበታል ። በሌላ በኩል ሃገር ለቀው ይወጡ የነበሩት ንጹሃን ዜጎች ብቻም አልነበሩም ። ለመሆኑ ጀርመናውያን በብዛት ሃገራቸውን ለቀው የተሰደዱባቸው ወቅቶች የትኛዎቹ ነበሩ ?
በቀደሙት ዘመናት ጀርመናውያን በብዛት ከተሰደዱባቸው ሃገሮች ውስጥ ዩናይትድ ስቴትስ በዋነኛነት ትጠቀሳለች ። ብዙዎች መጀመሪያ ከሚገቡባት ከኒውዮርክ ተነስተው በተለያዩ የአሜሪካን ግዛቶች ሰፍረዋል ። ከአሜሪካን ሌላ ካናዳ አርጀንቲና ብራዚል አውስትሬሊያ ና ኒውዚላንድም ጀርመኖች ከፈለሱባቸው ሃገራት ውስጥ ይገኛሉ ። ጀርመኖች በብዛት አሜሪካን ለመሰደዳቸው ብዙ ማሳያዎች አሉ ።
ሂሩት መለሰ
ተክሌ የኋላ