1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የብሔር ብሔረሰቦች ዕለትና የጀርመናዊቱ ባለሙያ አስተያየት

ማክሰኞ፣ ኅዳር 29 2002

ከአስራ-ሥምንት አመት በፊት ከነበረዉ ጋር ሲነፃፀር ብዙ እድገት ታይቷል።ኢትዮጵያ ብዙ ነገር አድርጋለች።እና ኢትዮጵያ በጥሩ ጎዳና ላይ ናት ብዬ አስባለሁ

https://p.dw.com/p/KxKg
ምስል AP

በኢትዮጵያ የብሔር ብሔረሰቦች ዕለት መከበሩ የሐገሪቱን ሕዝብ ለማስተዋወቅ፥ አንድነትና መቻቻልን ለማዳበር እንደሚረዳ ጀርመናዊቷ የፖለቲካ አዋቂ ገለጡ።የኢትዮጵያ የፌደረሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አማካሪ ዶክተር ፔትራ ሲመርማን ሐርትሽታይን ዛሬ ለአራተኛ ጊዜ የተከበረዉን የብሔር፥ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን አስታከዉ እንደተናገሩት ዕለቱ የተለያየ ባሕል፥ ቋንቋና እምነት ያላቸዉ የኢትዮጵያዉያንን ለማስተዋወቅና ለማቀራረብ ይጠቅማል።ዶክተር ሲመርማን ሽታይን ሐርትን ነጋሽ መሐመድ በስልክ አነጋግሮቸዋል።

እሳቸዉም እዚያዉ ድሬዳዋ የድግሱ ታዳሚ ናቸዉ።«በአሉ»-አሉ በኢትዮጵያ ሕዝብ ዘንድ ትርጉም ያለዉ መሆኑ አያጠያይቅም።ምክንያቱም፣-ቀጠሉ።«ምክንያቱም ጎሶች፥ብሔር፥ ብሔረሰቦች ምን አይነት ባሕል እንዳላቸዉ፥የትኛዉ አይነት ሙዚቃ እንዳላቸዉ የሚያሳዩና የሚያዩበት በመሆኑ ነዉ።አንዱ ከሌላዉ ጋር የበለጠ ይተዋወቅበታልም ብዬ አስባለሁ።»

ኢትዮጵያ በጎሳ ላይ የተመሠረተ ፌደራላዊ የፖለቲካ ሥርዓት መከተል ከጀመረች ከአስራ-ስምንት አመት በሕዋላ አሁን፣-የሐገሪቱን የዲሞክራሲ፥ የሰብአዊ መብት እና የልማት ይዞታን እንዴት-ይገመግሙታል? ጥያቄዬ ነበር።መለሱ ጀርመናዊቷ ባለሙያ-ብዙ እያሉ፥-

«ከአስራ-ሥምንት አመት በፊት ከነበረዉ ጋር ሲነፃፀር ብዙ እድገት ታይቷል።ኢትዮጵያ ብዙ ነገር አድርጋለች።እና ኢትዮጵያ በጥሩ ጎዳና ላይ ናት ብዬ አስባለሁ።»

ብዙ አለም አቀፍ የፖለቲካ ታዛቢዎችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ግን በዚሕ አይስማሙም። «ኢትዮጵያ ዉስጥ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት አለ፥ በሥልጣን ላይ ያለዉም አንባገናናዊ ሥርዓት ነዉ በማለት ይወቅሳሉ፥ አንዳዶቹም ይከሳሉ-ለሚለዉ ጥያቄዬ መልሳቸዉ አጭር-ደግሞም እቅጩን አይነት ነበር።

«ይሕን አስተያየት አልጋራም»

የሚል ዶክተር ፔትራ ሲመርማን ሽታይን ሐርት የዛሬዉን የድሬዳዋ በአል-ደማቅ ይሉታል

«በአሉ ጠዋት ከባዕሉ ማዕከላዊ ሥፍራ-ድሬዳዋ ስታዲዮም ዉስጥ ተጀመረ።እዚያ ሰማንያዎቹ ብሔር ብሔረሰቦች ተሰብስበዉ ነበር።ትርኢታቸዉን ለተጋባዥ እንግዶች አሳይተዋል።በቀጥታ በቴሌቪዥን ይተላለፍ ነበር።ደማቅና በቅይጥ ቀለም ያሸበረቀ ነበር።»

በበአሉ ላይ የብሩንዲ፥የሩዋንዳ፥ የኬንያ፥ የጅቡቲ የሶማሊ ላንድ እና የሌሎችም ሐገራት ባለሥልጣናት መገኛታቸዉን ዶክተር ሲመርማን ሽታይን ሐርት ገልፀዋል።እንዲሕ አይነቱ ትርዓትና ድግስ ሰላም፥ አንድነት፥ መቻቻልን ለማስፈን-ምን ይፈይዳል-ለሚለዉ ጥያቄ መልሳቸዉ ረዥም ነዉ።

«ከዚሕ በፊት የተከበሩትን ሰወስት በአላት ተመልክቻለሁ።አንድ ነገር ማረጋገጥ እችላለሁ።ብዙ ቡድናት ተለያይተዉ ነዉ-የሚኖሩት።አንዳዶቹ ደግሞ በጣም ሩቅ አካባቢ ሥለሚኖሩ አንዱ ከሌላዉ ጋር ለመገናኘት ሌላ አማራጭ የላቸዉም።ማለት፥ አንዳቸዉ ሥለ ሌላቸዉ ሊሰሙ ይችላሉ፥ የሚያዉቁበት አጋጣሚ ግን የላቸዉም።የብሔር ብሔረሰቦች ቀን አንዱ ከሌላዉ ጋር እንዲተዋወቅ፥በጋራ እንዲያከብሩም አንድ አጋጣሚ ነዉ።አንዱ የሚያደርገዉን ሌላዉ የሚያይበት ነዉ።አንዱ ሥለሌላዉ ምንነት የሚረዳበት ነዉ።አንዱ ከሌላዉ ጋር ይበልጥ የሚቻቻልበት፥የሚከባበርበትም ነዉ።የበአሉ አብይ መፈክርም---»

ባማርኛዉ አሉት-ጀርመኗ

እና ይሕ ጥሩ መልዕክት ነዉ-ይላሉ።ምክንያትም አላቸዉ።

«ምክንያቱም ያለመቻቻል ሥለ ዲሞክራሲ መናገር ከባድ ነዉ።ያለ መቻቻል አድነት መፍጠርም ከባድ ነዉ።ሰወስቱ ከሌሉ ደግሞ ልማት የለም።»

እንደገና ባማርኛ መልዕክት አላቸዉ።ከፈገግታ ጋር።ዶክተር ፔትራ ሲመርማን ሽታይንሐርት።

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ