1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቤተ እሥራኤላውያን ብሶት፣ ትግላቸውና ተስፋቸው

እሑድ፣ ግንቦት 2 2007

በመጽሐፍ ቅዱስ ከብሉይ ኪዳን እንደተገለጠው፣ ከአብርሃም ልጅ ከይስሐቅ የተወለደው ያዕቆብ፤ በኋለኛ ስሙ እሥራኤል፣ ካፈራቸው 12 ልጆች መካከል የ9ኛው ልጅ የዳን ዝርዮች ስለመሆናቸው ይነገርላቸዋል፦ ኢትዮጵያውያኑ ይሁዲዎች ወይም ቤተ እሥራኤላውያን

https://p.dw.com/p/1FNA4
ምስል Reuters/Baz Ratner

ለአያሌ ምዕተ ዓመታት በሰሜን ምዕራብና ሰሜን ኢትዮጵያ ፣ ከደምቢያ - ጎንደር እስከ ሽሬ- ትግራይ ፣ ከ500 በላይ በሚሆኑ የተለያዩ ትንንሽ መንደሮች ሠፍረው ይኖሩ የነበሩት እነዚሁ ቤተ እሥራኤላውያን፤ በእሥራኤል መንግሥትና በዩናይትድ ስቴትስ ይሁዲዎች ድጋፍ ወደ ቃል ኪዳን ሃገራቸው ከተጓዙ በኋላ በሃይማኖታቸው ረገድ ምንም እንኳ አንዳንድ አከራካሪ ሁኔታዎች እንዳጋጠሟቸው ቢገለጽም፤ በዓለም ዙሪያ ተበትነው ከኖሩ የይሁዲ ማሕበረ ሰቦች መካከል ፤ ሃይማኖቱ የሚያዘውን የኦሪትን ሕግ በመጠበቅ የኢትዮጵያዎቹ በግንባር ቀደምትነት እንደሚጠቀሱ ነው የሚነገረው።

Benjamin Netanjahu und Damas Pakada
ምስል picture-alliance/AA/Haim Zach

በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ ይሁዲዎች ፣ ወደ እሥራኤል የሚመለሱበት ሕገ - ደንብ፤ ቤተ እሥራኤላውያንን ጭምር እንደሚመለከት፣ የእሥራኤል መንግሥት፤ እ ጎ አ መጋቢት 14 ቀን 1977 ዓ ም፤ በይፋ አስታወቀ። አማርኛና ትግርኛ ተናጋሪዎቹ ፤ ለሃይማኖታዊ አገልግሎትም ግዕዝና ዕብራይስጥ ይጠቀሙ የነበሩት ቤተ እሥራኤላውያን ፤ እ ጎ አ ከ 1980ኛዎቹ ዓመታት አጋማሽ ገደማ አንስቶ ብዙ ወጪ በተደረገባቸው አስቸጋሪ በሆኑ የማሸጋገሪያ የጉዞ መርሐ ግብሮች ነበረ ፣ በሱዳንና በቦሌም በኩል በብዛት እሥራኤል የገቡት። እዚያ ደርሰው ዜግነታቸውን ካረጋገጡበት ጊዜ አንስቶ፣ ባለፉት 30 ዓመታት ፣ ከሕብረተሰቡ ጋር በመቀላቀል በአዲስ ሀገር ፣ አዲስ የተስተካከለ ሕይወት ለመምራት ፣ ከሕብረተሰቡና ከመንግሥት ተቋማት ሳይቀር የተለያዩ አግላይ ችግሮች እንዳጋጠሟቸው በየጊዜው ቢገልጹም፤ ድርጊቱን አምርረው በመቃወም አደባባይ ሲወጡ ከወዲያኛው ሰሞን በኢየሩሳሌምና ቴልአቪቭ የታየው የመጀመሪያ ባይሆንም አየል ያለ እንደነበረ፣ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኀን ዘግበውበታል። በእሥራኤል የተለያዩ የማሕበረሰብ ክፍሎች እዚህም ላይ የኢየሩሳሌሙ የ«ሂብርው» ዩንቨርስቲ ተማሪዎች አድልዎንና ዘረኝነትን በመቃወም ከቤተ- እሥራኤላውያን ጎን መቆማቸውን አሣይተዋል። የቤተ እሥራኤላውያን ችግር ሥረ-መሠረት ምን ይሆን? አብነቱስ?

ተክሌ የኋላ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ