የቤተሰብ ምጣኔ ጥረት
ማክሰኞ፣ ኅዳር 3 2006የቤተሰብ ምጣኔ ላይ የሚያተኩር ዓለም ዓቀፍ ጉባኤ በዛሬዉ ዕለት አዲስ አበባ ላይ ተጀምሯል። እስከ ሐሙስም ይዘልቃል። ባለፉት ዓመታት ጉባኤዉ በሌሎችም የአፍሪቃ ሃገራት የተካሄደ ሲሆን ኢትዮጵያ ስብሰባዉን ስታስተናግድ የመጀመሪያ ነዉ።
የመጀመሪያዉና በጎርጎሪዮሳዊዉ 2009ዓ,ም የተካሄደዉ ጉባኤ አስተናጋጅ ሀገር ዩጋንዳ ስትሆን ሁለተኛዉ ደግሞ ከሁለት ዓመታት በፊት ሴኔጋል ዉስጥ ተካሂዷል። ኢትዮጵያ ዘንድሮ ለዚህ ጉባኤ አስተናጋጅነት የተመረጠችዉ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ለማዳረስ ባሳየችዉ ቁርጠኛነት መሆኑ ነዉ የተገለጸዉ።
የቤተሰብ ቁጥርን የመመጠን ዉሳኔ የእያንዳንዱ ቤተሰብ ፍቃድና ፍላጎት ላይ የተመሠረተ መሆኑ ይታመናል። በዓለም ዓቀፍና ሀገር ዓቀፍ ደረጃ የሚደረጉ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት አቅርቦቶችም በማስተማርና ኅብረተሰቡን በማሳመን ላይ እንደሚያተኩሩ ነዉ በመስኩ የተሰማሩ ወገኖች የሚገልፁት።
የቤተሰብም ምጣኔ ወይም የልጆችን ቁጥር መመጠን ያስፈለገበት ምክንያት በአዳጊ ሃገራት ለሚገኙ ለበርካታ ወላጆች ዛሬም እንቆቅልሽ የሆነበት ሁኔታ መኖሩ አይካድም። ለዚህ ማሳያዉ ደግሞ ብዙዎች ዛሬም የወሊድ መከላከያን ለመጠቀም ፈቃደኝነት አለማሳየታቸዉ ነዉ። በእርግጥ ዘንድሮ አዲስ አበባ ላይ የሚስተናገደዉ ዓለም ዓቀፍ የቤተሰብ ምጣኔ ጉባኤ አገልግሎቱ ለሁሉም እንዲዳረስ እና በሙሉ ፈቃደኝነትም ሰዎች እንዲጠቀሙበት የሚለዉን ሃሳብ መመሪያዉ ነዉ። ዝርዝሩን ከድምፅ ዘገባዉ ያድምጡ
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ