የባለሃብቶች የካሣ ጥያቄ
ዓርብ፣ መጋቢት 9 2008ንብረተቸዉ ላይ ጉዳት የደረሰ የአገር ዉስጥም ሆና የዉጭ ባለሃብቶች የኢትዮጵያ መንግሥት ካሣ እንዲከፍላቸዉ መጠየቃችሁን በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ጌታሁን ነጋሽ ለዶቼ ቬሌ ገልጸዋል። ካሣዉን ለመክፈል የኮሚሽኑ ቦርድ የጉዳቱን መጠንና በምን መልክ መስተናገድ እንደሚገባ እያጠና መሆኑንና ዉሳኔዉን እየተጠባበቁ መሆናቸዉንም አቶ ጌታሁን ጨምረዉ ያስረዳሉ።
በኦሮሚያ ክልል ለተቀዉሞዉ መንስኤ ከሆኑት አንዱ በግብርና የሚተዳደሩ የክልሉ ነዋሪዎች በኢንቨስትመንት ስም ቦታቸዉን ካለፍላጎታቸዉ እና ያለ በቂ ካሣ እንዲለቁ በመደረጋቸዉ እንደሆነ ዘገባዎች ያመለክታሉ። በተቃዉሞ እንቅስቃሴ ከመንግሥት ኃይሎች ጋራ በተፈጠረዉ ግጭትም ለባለሃብቶች በተሰጡ ቦታዎች ላይ ጥቃት እንደደረሰ እና ነዋሪዎችም መሬታቸዉን መልሰዉ እንደተረከቡም ተሰምቶዋል። ኅብረተሰቡና መንግስት መካከል አለመግባባት ሲፈጠር የመንግሥት ተቋማት እና የኢንቬስትመንት ዘርፎች ላይ ጉዳት መድረሱ እንደሚጠበቅ አቶ ጌታሁን ይጠቁማሉ።
እንዲጠቀስ ያልፈለጉት የመቱ፣ ኢሉባቦር፣ ነዋሪ የሆኑ ግለሰብ የግጭቱ ሰበብ እና መንስኤ ከመንግሥት በኩል ያለዉ ወቅታዊ ሁኔታ በመሆኑ መንግሥት ካሣ የመክፈል ኃለፊነት አለበት ይላሉ። ዋናዉ ጉዳይም ካሣዉ ይከፈል አይከፈል የሚለዉ ሳይሆን ይላሉ አስተያያት ሰጭዉ፤ ለተፈጠረዉ ቸግር መቋጫዉ ምን መሆን አለበት ነዉ ስሉ ጠይቀዋል። እንደእሳቸዉ አባባልም ለተነሳዉ ተቃዉሞ መሬት አንድ ምክንያት ቢሆንም ኅብረተሰቡ መንግስት ላይ ያለዉ ብሶት እና በየጊዜዉም የሚወጡ ኅብረተሰቡ የማይቀበባቸዉ ፖሊዎች እና ሕጎችም መንስኤዎች ናቸዉ ብለዋል።
ዘመኑ ታፈረ የጤና ባለሙያ እና የጎጃም ነዋሪ ናቸዉ። በአገሪቱ ዉስጥ ያሉት ኩባንያዎች መንግሥን አምነዉ እየሠሩ በመሆኑ መንግሥት ከለላ እንዲሰጣቸዉ ነዉ የሚያሳስቡት። በዶቼ ቬሌ የፌስቡክ ደረ ገፅ ላይ ይህን ጉዳይ አስመልክቶ በተደረገዉ ዉይይት አብዛኞቹ መንግሥት ንብረታቸዉ ለተጎዳ ካሣ መክፈል እንዳለበት ጠቁመዉ፤ የጠፋዉ የሰዉ ሕይወትስ እንዴት ሊካስ ይቻላል? ሲሉም ጠይቀዋል።
መርጋ ዮናስ
ሸዋዬ ለገሠ