1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የባህል መድረክ

ሐሙስ፣ መጋቢት 13 2004

የለቱ ቅንብራችን የዶይቼ ቬለ የባህል ድረ-ገጽ ካተኮረባቸዉ ርዕሶች መካከል ሁለት ርዕሶችን መርጦ ይዞአል። በሶማልያ መዲና መቃዲሾ ከሃያ አመታት በላይ ስራዉን ያቋረጠዉ የባህል መድረክ ዳግም ስራ መጀመሩን የሚያሳይ ሲሆን ሁለተኛዉ ርዕስ በአፍሪቃ የማይገኙ ግን አፍሪቃ የተሰሩ የሙዚቃ ሃብቶች በጀረመን ግዙፍ የሙዚቃ ማህደር መገኝታቸዉ የሚል ነዉ

https://p.dw.com/p/14PJP
በጀርመን በማይንዝ ከተማ የሚገኝዉ ከፍተኛ የሙዚቃ ክምትች ማዕከልምስል Hauke Dorsch

የለቱ ቅንብራችን የዶይቼ ቬለ የባህል ድረ-ገጽ ካተኮረባቸዉ ርዕሶች መካከል ሁለት ርዕሶችን መርጦ ይዞአል። የመጀመርያዉ ርዕስ በያዝነዉ ሳምንት መጀመርያ ጦርነት ባመሰቃቀላት የሶማልያ መዲና መቃዲሾ ከሃያ አመታት በላይ ስራዉን ያቋረጠዉ የባህል መድረክ ዳግም ስራ መጀመሩን የሚያሳይ ሲሆን ሁለተኛዉ ርዕስ በአፍሪቃ የማይገኙ ግን አፍሪቃ የተሰሩ የሙዚቃ ሃብቶች በጀረመን ግዙፍ የሙዚቃ ማህደር ተጠብቀዉ መገኝታቸዉ የሚል ነዉ

ከሁለት አስርተ አመታት በላይ መንግስት አልባ ሆና የቆየችዉ ሶማልያ አሁንም ስፊዉ ግዛትዋ ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት እንዳለዉ በሚነገርለት በአክራሪዉ ደፈጣ ተዋጊ ቡድን እጅ ስር ይገኛል። እንድያም ሆኖ ደፈጣ ተዋጊዉን ቡድን አሸባብን በአፍሪቃ ህብረት ሃይል የሚደገፈዉ የሶማልያ የሽግግር መንግስት ከመዲናዋ ከመቃዲሾ በርቀት ማባረሩ ይታወቃል። ከብዙ አመታት በኋላ ደግሞ በመዲናዋ በመቃዲሾ የሶማልያ ብሄራዊ ትያትር ቤት ስራ ጀምሯል። ይህም በአገሪቱ ሰላም የመስፈኑ ዉጋጋን ነዉ ስትል የዶይቼ ቬለዋ አንያ ዲክ ሃንስ ዘግባለች።

እንዲህ ያለዉ በባህላዊ ዉዝዋዜ የደመቀ ባህላዊ ሙዚቃ በመቃዲሾ በሚገኝዉ የሶማልያ ብሄራዊ ትያትር ዉስጥ ለህዝብ ከቀረበ ከሁለት አስርተ አመታት በላይ አስቆጠረ። ጦርነት ባመሰቃቀላት የሶማልያ መዲና ህይወትን ለማዳን እራስን ለመደበቅ ከሚደረግ ሩጫ በስተቀር በትያትር ቤት ገብቶ ለመዝናናት የማይታሰብ ነበር። በትያትር ቤቱ መድረክም ተዋንያን ትዕይንታቸዉን ለህዝብ ከማሳየት ይልቅ፤ መድረኩን የጦር አበጋዞች መኖርያቸዉ እና አደጋ ለመጣል መዘጋጃ ቦታቸዉ አድርገዉት ቆይተዋል ። በአንያ ዲክ ሃንስ ዘገባ መሠረት ከቅርብ ወራቶች ወዲህ መዲና መቃዲሾ አንፃራዊ ሰላም ያገኘች ይመስላል። በያዝነዉ ሳምንት ሰኞ መቃዲሾ የሚገኝዉ የሶማልያ ብሄራዊ ትያትር ቤት በደማቅ ስነ-ስርአት በሩን ለተመልካች ዳግም ከፍቷል ። በሰነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የሶማልያዉ ፕሪዚደንት ሼክ ሻሪፍ አህመድ የሶማሊያው ግጭት መቆም አለበት ሲሉ አሳስበዋል።

Somalia Mogadischu Kämpfe
ሞቃዲሾምስል Reuters

ዛሪ በዚህ ምሽት ላይ በመገኝቴ እጅግ ደስተኛ ነኝ። ህዝቡ ሁልግዜ በአገሪቱ ዉስጥ የደረሰዉን ዘግናኝ ሁኔታን እንዲያስብ ሳይሆን፣ በብሩህ ወደፊት እንዲመለከት የሆነ ነገር ልንሰራለት እንፈልጋለን። በአገሪቱ የሚታየዉ የሃይል እርምጃ እና ጥቃት ሊያበቃ ይገባል። እኛም አዲሱን የሰላም ዘመን ለጋራ እድገት በጋራ ሃሳብ እና ስሜት እንጀምራለን።

ሶማልያ ከአዘቅት ገና በማንሰራራት ላይ መሆንዋ፣ ዳግም የተከፈተዉን ብሄራዊ ትያትር አይቶ መፍረድ ይቻላል። የብሄራዊዉ ትያትር ቤት ጣርያ የለዉም ግድግዳዉ በሞርታር እና በጥይት ተበሳስቶአል፣ የትያትር ቤቱ እድምተኞች የመጀመርያዉን ትእይንት የተከታተሉት ላስቲክ ወንበር ላይ ተቀምጠዉ ነዉ።

«ትያትር ቤቱ በጦርነቱ እጅግ ተጎድቶአል። ለዚህም ነዉ ይህ ጉዳይ ትልቅ ትርጉም ያለዉ። የትያትር ቤቱ መልሶ መከፈት መቃዲሾ የ21 አመቱን ጦርነት ወደኋላ መጣልዋን አመላካች ነዉ»

ይላሉ የመቃዲሾ ከተማ አስተዳዳሪ ሞሃድ አህመድ ኑር፣ የሶማልያ የሽግግር መንግስት በአፍሪቃዉ ህብረት የጦር ሃይል በመታገዝ አክራሪዉን አሸባብን በማባረር ካለፈዉ የአዉሮጳዉያኑ ሐምሌ ወር ጀምሮ መቃዲሾን በቁጥጥር ስሩ አድርጎአል። ቀደም ሲል የአሸባብ ሚሊሽያዎች በከተማይቱ ዳንስ እና የሙዚቃ ዝግጅትን በጥብቅ ከልከለዉ ነበር። ቲያትር መጫወትም ከባድ ቅጣትን ያስከትል ነበር። ይህ ሁሉ አልፎ በመቃዲሾ የሚገኝዉ ብሄራዊ ትያትር የመጀመርያውን የመድርክ ዝግጅት ለማቅረብ መብቃቱ ለብዙ ታዳሚዎች ልክ እንደ ነጻ መዉጣት ያህል ነበር። አንዳንዶች በደስታ አልቅሰዋል

Somalia Konferenz London 2012 Präsident Somalia Sharif Ahmed und Premierminister Abdiweli Mohamed Ali
የሶማልያዉ ፕሪዝደንት እና ሽሪፍ አህመድ እና ጠ/ሚ አብዲቫሊ መሃመድ አሊምስል REUTERS

«ደስታዬ ወሰን ያለፈ ነዉ። በ 70ዎቹ አመታት ብዙግዜ የዚህ ትያትር ቤት ታዳሚ ነበርኩ። በርካታ የአገሪቷ ታዋቂ ሙዚቀኞች በትያትር ቤቱ የሙዚቃ ድግሶቻቸዉን ያሳዩ ነበር። ከነዝያ ሙዚቀኞች መካከል አሁን በህይወት ማን እንዳለ እንኳ በፍጹም አላዉቅም»

የመቃዲሾዉ ብሄራዊ ትያትር ከሃያ አንድ አመት በኋላ የመጀመርያ ትእይንት የጦርነት እና የአሸባሪነትን አስከፊነት የሚዳስስ ነበር። የቀረበዉ ተዉኔት ሃዘን ያጠላበት ብቻ ሳይሆን አንዳንድ የሚያስቁና ፈገግ የሚያደርጉ ትዕይንቶችም ተካተዉበታል።

የመቃዲሾዉ ብሄራዊ ትያትር በቀጣይ እድምተኞቹን አሰባስቦ የሙዚቃ ድግሱን ለመሳየት በዕቅድ ላይ ነዉ። መድረኩና የትያትር ቤቱ ህንጻም እድሳት እንደሚደረግለት ተመልክቶአል። ትያትር ቤቱ ከሃያ አንድ አመት በኋላ ያዘጋጀዉ መድረክ ላይ የተገኙ መቃዲሽ ወደሰላማዊ ህይወት መመለስዋን አመላካች ነዉ ሲሉ ተናግረዋል።

«ይህ ማለት መጭዉ ህይወት ለኛ የተሻለ ነዉ ማለት ነው። ቲያትር ቤቱ ሲታደስም ቀሪዉ የከተማዉ ክፍልም ይሻሻላል»

የአፍሪቃ ሙዚቃ ክምችት በጀርመን ይላል ሁለተኛዉ ርዕሳችን

Universität Mainz Archiv für die Musik Afrikas
የአፍሪቃ የሙዚቃ ክምትች ማዕከልምስል DW

በጀርመን የራይን ላንድፋልዝ ክፍለ ግዛት መዲና በሆነዉ በማይንዝ ከተማ የሚገኝዉ ከፍተኛ የሙዚቃ ክምትች ማዕከል ፣ ከአለም ዙርያ በርካታ ሙዚቃዎችን በማሰባሰብ ፣ ታላቅ የአለም ታሪክን የያዘ ሃብት መሆኑ ይነገርለታል። ከ 20 አመታት በፊት ከአፍሪቃዊትዋ ጋና 500 የሙዚቃ አልበሞች በመሰብሰብ ስራውን የጀመረዉ ይህ ማዕከል ዛሪ ከፍተኛ የአፍሪቃ ሙዚቃ ክምችት አለው። ከአፍሪቃ የተገኘው ከጃዝ፣ እስክ,ሂፕ ሆፕ ከሶል እስከ ፖፕ ሙዚቃ ግዙፍ ስብስብ ከገሚስ በላይ በራስዋ በአፍሪቃ ለመድሃኒት እንደማይገኝ ተጠቅሷል። የዶይቼ ቬለዋ አና ካትሪን የማይንዙን የአፍሪቃ የሙዚቃ ማዕከል ጎብኝታ በጻፈችዉ ዘገባዋ መጀመርያ በዚህ ተቋም የሚገኝዉን ልዩ እና ግዙፍ የሆን ቦታ ታስተዋውቃለች ። ልዩ የአፍሪቃ ሙዚቃ ክምችት የሚገኘው ምድር ቤት ነው። 5 ጥብቅ በሮችን አልፎ ነዉ የሶል የሪጌ የሂፕሆፕ እና የጃዝ ሙዚቃ ክምችቱ የሚገኝዉ።

በርካታ ኢትዮጵያዉያን ዘፋኞችሙዚቃዎቻቸውን በካሴት አሳትመዋል። ከነዚህም አንዷ እንደዚህ ጽሁፍ አቅራቢ አና ካትሪን አገላለጽ አሜሪካዉያን «የሶል ሙዚቃ ንግሥት» ብለዉ እንደሚጠሯት አሪታ ፍራንክሊን ያህል በአፍቃሪዎቿ የምትደነቀው አስቴር አወቀ ናት ። አስቴር በ 70 ዎቹ እና በ 80 ዎቹ በርካታ ሙዚቃዎቿን በካሴት አሳትማለች። የጀርመንና የኢትዮጵያ ወዳጅነትን ከ 100 ዓመት በላይ መሆኑን ነጋድራስ ተሰማ እሽቴ የዛሬ 115 ዓመት ግድም ጀርመን ውስጥ በሸክላ ያስቀርጹት የማሲንቂ ዜማ አንዱ ምስክር ነዉ። ጀርመናዊዉ የሙዚቃ ፕሮፊሰር ዎልፍ ጋንግ ቤንደር ጥንታዊ የአፍሪቃ ሙዚቃዎችን በማሰባሰባቸዉ ዝናን አትርፈዋል። በሙዚቃ ትምህርት የዶክትሪት ማዕረጋቸዉን የያዙትና በበርሊን ነዋሪ የሆኑት ዶክተር ትምክህት ተፈራ በማይንዙ ግዙፍ የሙዚቃ ማህደር ሰርተዋል ብዙ ጽሁፎችንም አቅርበዋል። በማይንዝ ግዙፍ የሙዚቃ ማህደር ምን ያህል የኢትዮጵያ ጥንታዊም ሆኑ ዘመናዊ ሙዚቃዎች ይገኛሉ። ዝርዝሩን ያድምጡ!

አንያ ዲክ ሃንስ

አዜብ ታደሰ

ሂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ