የሼል ኩባንያ ችሎት በደን ኻግ
ሐሙስ፣ ጥቅምት 1 2005በአውሮፓ፣ ዘይት ወደ አከባቢ ተለቆ የባህር ዳርቻን ሲያቆሽሽ ፣ በርግጠኝነት ህግ ፊት ቀርቦ ውሳኔ በኒጀር ዴልታስ አከባቢውን በሙሉ ያበላሸ የዘይት ብከላ እንዴት ይታይ ይሆን? ለዚህ በናይጄርያ ተፈጥሯል ለተባለው ያከባቢ ብክለት ተጠያቂ ነው የሚል ክስ የቀረበበት የ ሼል ኩባኒያው ችሎት ዛሬ በኔዘርላንድ ፍርድ ቤት ቀርቦ መልስ ሰጥቷል።
በኒጄር ዴልታ የሚገኙ ወንዞችና ሓይቆች ከዚህ በፊት በአከባቢው የሚኖሩ አርሶ አደሮችና በአሣ ምርት የሚተዳደሩ ሰዎች የህይወት ምንጭ ነበሩ። ዛሬ ግን ቦታው በነዳጅ ዘይት ዝቃጭ ተበክሏል። ሃምሳ ዓመት ያስቆጠረው ይህ የነዳጅ ዘይት ምርት ባስከተለው መዘዝ ምክንያት፣ አከባቢውን መልሶ የማጽዳቱ ሥራ 30 ዓመት እንደሚወስድና እስከ አንድ ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንደሚያስወጣ፣ ከዓመት በፊት በተባበሩት መንግስታት የተሰራ አንድ ጥናት ያመለክታል። ለዚህ የአከባቢ ብከላ ኃላፊነቱን የሚወስድ ማነው?
«ሁለት የአሰራር መስፈርት ያላቸው የሚመስሉ እንደ ሼል ያሉ ድርጅቶች በአውሮፓና እንደ ናይጄሪያ ባሉ ሀገራት፣ የሚከተሉት አሰራር እጅግ የተለያየ ነው። አንድ የነዳጅ ዘይት ኩባንያ የእርሻ መሬትን በዘይት ዝቃጭ ማቆሸሽ እንዲቆም እርምጃ ሳይወስድ የሚያልፍበት ሁኔታ አውሮፓ ውስጥ ከቶውኑ አይታሰብም። ግን ናይጄሪያ ውስጥ ይህን ማድረግ ችሎዋል። በዚህ መልኩ ነው አንድ ኩባኒያ ያከባቢ መጠበቂያ መስፈርቶችን ችላ ማለት የሚጀምረው።»
በዚህ ምክንያት ነው ሚልዬ ዴፎንሲ በተባለ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት የሚሰሩት ጊርት ሪትሴማ፣ ከአራት የናይጄሪያ አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በሼል ኩባኒያ ላይ ክስ የመሰረቱት። ጥያቄያቸውም፣ አከባቢውውን የሚበክል የነዳጅ ዘይት መንጠባጠብን ለማስቆም አዲስ ማስተላለፊያ ቧንቧዎች እንዲሰሩና አከባበው በተገቢው እንዲጸዳ፣ እንዲሁም መታዳደሪያ ስራቸውን በነዳጅ ዘይቱ ምክንያት ላጡ ያከባቢው አርሶ አደሮችና አሳ አጥማጆች ካሳ እንዲከፈል ነው።
አንድ ኩባንያ በሌላ ሀገር ውስጥ ለፈጸመው ጥፋት ፍርድ ቤት መቅረቡ በአውሮፓ የታዋቀ አይደለም። የህጉ ጉዳይ ብዙውን ጊዜ ግልጽ አይደለም። የአውሮጳ ፍርድ ቤት ለመሆኑ አውሮጳ ውስጥ ያልተከሰተውን የክስ ጉዳይ ለመመልከት ለመሆኑ ኃላፊነቱ አለው? እንዲህ አይነት የፍርድ ሂደት ከፍ ያለ ወጪ የሚያስወጣ ብቻ ሳይሆን፣ ሌሎች ብዙ እንቅፋቶች አሉት ይላሉ በጀርመኑ ኡትሬችት ዩኒቨርስቲ የህግ ባለሙያዋ ሊስቤት ኤኔኪንግ፣
«አብዛኞቹ ማስረጃዎች ያሉት በከሳሹ ሳይሆን በተከሳሹ ኩባኒያ እጅ ነው። ለምን ነዳጅ ዘይቱ ተንጠባጠበ?፣ የነዳጅ ዘይት መተላለፍያ ቧምቧዎች በምን ያክል ጊዜ ውስጥ እድሳት ይደረግላቸዋል? የተበላሹት በጥንቃቄ ጉድለት ነው ወይስ ሆን ተብሎ ነው? ሼል፣ ነዳጅ ዘይቱ ወደ አከባቢው ከመፍሰሱ በኋላ ዬትኞቹን እርምጃዎች ወስዷል? የሮያል ደች ሼል ኩባኒያ በናይጄሪያ ስለሚገኘው የዘይት መተላለፍያ ቧምቧ አያያዝ ላይ ምን አይነት ተጽዕኖ አለው ለሚሉ ጥያቄዎች ማስረጃ ያስፈልጋል።»
ሼል እነኚን ጥያቄዎች በፍርድ ሂደቱ ውስጥ መመለስ ይገበዋል። ኩባኒያው በኔዘርላንድ እየተካሄደ ያለውን የህግ ሂደት ወደ ናይጄሪያ ፍርድ ቤት እንዲዞርለት ሞክሯል። <<ተጠያቂው በናይጄሪያ የሚገኘው የሼል እህት ኩባኒያ ነው>> የሚለውን የሼል ክርክር፣ የሄጉ ፍርድ ቤት ዳኛ ውድቅ አድርገዋል።
«በኔዘርላንድስ በሚገኘው የሮያል ደች ኩባኒያ ብቻ ሳይሆን፣ በናይጄሪያ የሼል እህት ኩባኒያም ለጉዳዩ ተጠያቂዎች መሆናቸውን ፍርድ ቤቱ አውጇል። ይህ ለሌሎቹም እንደ ምሳሌ ሊያገለግል የሚችል የህግ ጉዳይ ነው። አሁን በኔዘርላንድስ ፍርድቤት ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባኒውያን ሲከሰሱ እናት ኩባኒያ ብቻ ላይ ሳይሆን በሌላ ሀገር በሚገኝ እህት ኩባኒያ ላይም ክስ መመስረት ይቻላል።»
በአውሮፓ እንዲህ አይነት ክስ ከዚህ በፊት የታየው በአንድ የለንዶን ፍርድ ቤት ነበር። ብዙን ጊዜ ዓለም አቀፍ ግዙፍ ኩባኒያዎችን በተመለከተ የሚነሱ ክሶች የሚሰሙት ከወደ አሜሪካ ነው።
ዛሬ በተካሄደው የሄግ ፍርድ ቤት ውሎ በናይጄሪያ በዘይት ማስተላለፍያ ቧምቧዎች ላይ የደረሰ ብልሽት ሆን ተብሎ የተደረገ የማበላሸት እርምጃና በስርቆት ምክንያት ነው ሲል ሼል ኩባኒያ ተከራክሯል። የከሳሾቹ ጠበቃ ግን ቧምቧዎቹ ከጊዜ ርዝመት የተነሳ መዛጋቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል። የፍርድ ቤቱ የመጨረሻ ውሳኔ በያዝነው የፈረንጆች ዓመት መጨረሻ እንደሚሰጥ ይጠበቃል።
ቬራ ከርን
ገመቹ በቀለ
አርያም ተክሌ