የሶሻል ዲሞክራት ፓርቲ ለጥምር መንግሥት ተስማማ
ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 5 2006በጀርመን ምርጫ ከተካሄደ ከሶስት ወራት በኋላ ዛሬ ጀርመን ጥምር መንግሥት እንደሚኖራት ታዉቋል። በምርጫዉ የመጀመሪያዉን እና ሁለተኛዉን ደረጃ ከያዙት ከእህትማማቾቹ የክርስቲያን ዲሞክራቲክ ሕብረት እና የክርስቲያን ሶሻል ሕብረት (CDU/CSU) ጋር በመሆን የሶሻል ዲሞክራት ፓርቲ (SPD) ጥምር መንግሥት እንዲመሰርት የፓርቲው አባላት በሰጡት ድምፅ ተስማምተዋል። 470 000 ግድም ከሚሆኑት የሶሻል ዲሞክራት ፓርቲ አባላት ውስጥ 77 በመቶ የሚሆኑት በድምፅ አሰጣጡ ላይ የተካፈሉ ሲሆን፤ 23,5% ከመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው በጥምር መንግሥት ምስረታው ያልተስማሙት።
የድምፅ ቆጠራዉ ዛሬ ከሰዓት በኋላ ይፋ ቢሆንም የሶሻል ዲሞክራት ፓርቲ (SPD) ጥምር መንግሥት ለመመስረት እንደሚስማማ ከትዕናንት ማምሻውን ጀምሮ በርካታ የመገናኛ ብዙኃን በጥምሩ መንግሥት የሚያገኙትን የሚኒስትርነት ማዕረግ ስልጣን ድልድል ሲዘግቡ ቆይተዋል። በዚህም በሰረት የSPD ሊቀመንበር ዚግማር ጋብርኤል የኢኮኖሚና ኃይል ሚኒስትር፤ በጎርጎረሳዉያኑ ከ2005 እስከ 2009 ዓ,ም የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንደሚሆኑ ይፋዊ ያልሆኑ መረጃዎች እየጠቆሙ ነዉ። የሶሻል ዲሞክራቶች ባጠቃላይ ስድስት የሚኒስትር መሥርያ ቤቶችን እንደሚወስዱም ተገልሯል። የባቫርያዉ የክርስቲያን ሶሻል ሕብረት CSU ፓርቲ በአጠቃላይ ሶስት የሚኒስትር መስርያ ቤቶችን እንደሚይዝ ነዉ ይፋዊ ያልሆነዉ መረጃ የሚጠቁመዉ። የመርሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል የክርስቲያን ዲሞክራቲክ ሕብረት CDU ፓርቲ አምስት ሚኒስቴር መስርያ ቤቶችን እና የመራሂተ መንግስቱን ስልጣን እንደሚይዙም ተያይዞ ተዘግቧል። የሶሻል ዲሞክራት ፓርቲ SPD ሊቀመንበር ዚግማር ጋብርኤል ፓርቲያቸዉ ለጥምር መንግሥት መስማማቱን ሲያስታውቁ፤ « ይህ ለፓርቲዉ ራሱ ትልቅ ዉጤት ነዉ፤የዲሞክራሲ ድግስ ነዉ። ቀኑ በጀርመን በሶሻል ዲሞክራቶች ፓርቲ ብቻ ሳይሆን ፤ በጀርመን የዲሞክራሲዊ ሂደት ታሪክ ዉስጥም ተጠቃሽ የሚሆን ይመስለኛል» ሲሉ ተደምጠዋል።
ልደት አበበ
አዜብ ታደሰ