የሶሪያዉ ዉጊያና ዲፕሎማሲዉ
ሐሙስ፣ መስከረም 10 2005
የዘንድሮዉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላይ ጉባኤ የሶሪያዉ ጦርነት ሥለሚቆምበት ሁኔታ ልዩ ትኩረት ሠጥቶ እንደሚወያይ የድርጅቱ ዋና ፀሀፊ ፓን ጊ ሙን አስታወቁ።ፓን ሰሞኑን ኒዮርክ ዉስጥ ሥለሚጀመረዉ አመታዊ ጉባኤ ትናንት በሰጡት መግለጫ እንዳሉት ጉባኤዉ እየተባባሰ ከመጣዉ ከሶሪያ ቀዉስ በፊት የሚያስቀድመዉ የለም።የአዉሮጳ ሕብረትና የቻይና መሪዎችም ዛሬ ብራስልስ ዉስጥ ሥለ ሶሪያ ቀዉስ መነጋገራቸዉ ተዘግቧል።ዓለም አቀፉ የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አምንስቲ ኢንተርናሽናል በበኩሉ በሰላማዊ ሰዉ ላይ የሚፈፀመዉ ግድያ መባባሱን አስታዉቋል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ልዩ መልዕክተኛ ላሕዳር ብራሒሚ ደማስቆ ላይ የሞከሩት ድርድር፥ የግብፁ ፕሬዝዳት መሐመድ ሙርሲይ ከብራስልስ ያሰሙት ማስጠንቀቂያ፥ ሌላ ዲፕሎማሲ፥ ሌላ ማስጠንቀቂያ፥ ከማስከተል ባለፍ ሺዎችን የሚፈጀዉን ጦርነት ለማስቆም ጭላንጭል ተስፋ እንኳን አልፈነጠቀም።
ብራሒሚ ከደማስቆ ወደ ካይሮ ሲያቀኑ፥ ወደ ቤጂንግ ሔደዉ የነበሩት «የሶሪያ ብሔራዊ አካል ለዲሞክራሲያዊ ለዉጥ» የተሰኘዉ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ሐሰን አብድል አዚም ወደ ደማስቆ ይዘዉት የተመለሱት ነገር ምንነት በዉል አልታወቀም።የሶሪያን መግሥት በሐይል ለማስወገድ የሚፋለሙት አማፂያንም፥ የሶሪያ መንግሥትም በመጥፎ የሚያይዋቸዉ ሐሰን አብድል አዚም የቻይናዉን ጠቅላይ ሚንስትር ማነጋገር አለማነጋገራቸዉም ግልፅ አይደለም።
ጠቅላይ ሚንስትር ዌን ጂያባኦ ግን ዛሬ ብራስልስ ዉስጥ ከአዉሮጳ ሕብረት ባለሥልጣናት ጋር ከተነጋገሩበት ጉዳይ አንዱ የሶሪያ ግጭትና ጦርነት ነዉ።የአል-አሰድ ደጋፊ የምትባለዉ የቻና ጠቅላይ ሚንስትር ዌን ዛሬ ያነጋገሩና የሚያነጋግሯቸዉን የአዉሮጳ ሕብረት መሪዎች ባለፈዉ ሳምንት ያነጋገሩት የግብፁ ፕሬዝዳት መሐመድ ሙርሲይ ካይሮ ላይ የኢራን፥ የቱርክና የሳዑዲ አረቢያን ባለሥልጣናትን ዛሬ ለዉይይት ጋብዘዋል።
የዉይይቱ ርዕሥ። ሶሪያ።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን የድርጅታቸዉ አመታዊ ጉባኤ ከሶሪያ ቀዉስ በፊት የሚያስቀድመዉ የለም ያሉት፥ የዌን የብራልስ ጉብኝት፥ የካይሮዉ ስብሰባ ዛሬ ከመጀመሩ በፊት ነበር።ትናንት
«እየተባባሰ የመጣዉ የሶሪያ ሁኔታ ከሁሉም በላይ በአዕምሯችን የተያነዉ ጉዳይ ነዉ። እንደምታዉቁት የጋራ ልዩ መልዕክተኛ ላሕዳር ብራሒሚ በሶሪያ የሽግግር ሒደትን ለማስጀመር የሚያደርጉት ዲፕሎማሲያዊ ጥረት እንደቀጠሉ ነዉ።ፕሬዝዳት አሰድንና የተቃዋሚ መሪዎችን ባለፈዉ ሳምንት አነጋግረዋል።ከዚሁ በተጓዳኝና ልዩ ትኩረት በመስጠት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሶሪያ ዉስጥና ባካባቢዉ ሰዓት በሰዓት ሰብአዊ ርዳታ እሰጠ ነዉ።»
የመመካከለኛዉ ምሥራቅ ታዛቢዎችን ትኩረት የሳበዉ ግን ከፓን መግለጫ ይልቅ የካይሮዉ ስብሰባ አለማና ስብጥር ነበር።የበሽር አል-አሰድን መንግሥት በነፍጥ ለማስወገድ የሚፋለሙትን ሐይላት የሚያስታጥቁት ሳዑዲ አረቢያና ቱርክ፥ ግብፅን መሐል አድርገዉ የበሽር አል-አሰድን መንግሥት ከሚደግፉት ኢራኖች ጋር መወያየት መቻላቸዉ በርግጥ አጓጊ ነበር።ሪያዶች እንደጓጓችሁ ቅሩ ብለዉ ነዉ መሰል ከስብሰባዉ ቀሩ።
ሶሪያ ያዉ ትጋያለች።ሕዝቧም ይረግፋል።የዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት የአምንስቲ ኢንተርናሽናል አጥኚ ዶናቴሌ ሮቬራ እንደሚሉት የሰላማዊዉ ሕዝብ ስቃይ እጅግ ብሷል።
«በሐያ ስድስት ከተሞችና መንደሮች እንያዳዳቸዉ በዘፈቀደ ካዉሮፕላን በሚጣሉ ቦምቦችና በሚተኮሱ መድፎች መደብደባቸዉን የሚያረጋግጥ መረጃ አግኝቻለሁ።እንዲሕ ዓይነቱ ጥቃት በተለያዩ አካባቢዎች በየዕለቱ ሲደርስ አይቻላሁ።ብዙ ጊዜ የሰዉ ሕይወትና አካል ያጠፋሉ።ሟች ቁስለኞቹ ደግሞ ሠላማዊ ሰዎች ናቸዉ።»
የሰላማዊ ሰዎች እልቂት ዛሬም እንደመሰባቸዉ ቀጥሏል።የመንግሥት የጦር ጄቶች ራቅ በተባለዉ አካባቢ የጣሉት ቦምብ አንድ ነዳጅ ማከማቻ አጋይቷል።ቃጣሎዉ ከሰላሳ በላይ ሰዉ ገድሎ፥ ሰባ ያሕል አቁስሏል።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ