የስምጥ ሸለቆው እሳተ ገሞራዎች አዲስ ጥናት
ረቡዕ፣ ጳጉሜን 5 2006እንደሚጠቁመው በኢትዮጵያው ስምጥ ሸለቆ አካባቢ 50 ሚሊዮን ገደማ የሚሆን ህዝብ ደረጃውም ሆነ መጠኑ ለማይታወቅ የእሳተ ገሞራ አደጋ ተጋላጭ ሆኖ ይኖራል። ይሁንና ፣ ምንና መቼ ሊያጋጥም እንደሚችል ፣ በሥጋት ከመተንበይ በስተቀር በትክክል የሚያውቅ ያለ አይመስልም።
በኢትዮጵያው ስምጥ ሸለቆ ከዚህ ወር አንስቶ በሚመጡት አምስት ዓመታት በእቅድ መሠረት ስለሚካሄድ ጥናትና ግብ ፣ የአንድ ባለሙያ ማብራሪያ አለን።
በዛ ያሉ የውጭ ሀገራትን ተመራማሪeዎች ጭምር የሚያማልሉ የከሰሙና ያልበረዱ እሳተ ገሞራዎች መኖራቸው እሙን ነው። ኣንዳንዴ አደጋ ማስከተል መቻላቸው ብቻ ሳይሆን ፤ ሰፊ ጠቀሜታ ስለሚሰጡት እሳተ ገሞራዎች፤ ብዛትና ዓይነት ፤ በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ፤ የሥነ ምድር ሳይንስ መምህር ፣ ፕሮፌሰር ገዛኸኝ ይርጉ --
ከዚህ ቀደም ከ 5 ዓመት በላይ መቅድማዊ ፕሮጀክት አፋር መስተዳድር ውስጥ ጋባሁ በተባለ አካባቢ በ 1998 (እ ጎ አ በ 2005 )በመስከረም ወር ላይ ከፍተኛ የምርምር እንቅሥቃሴ ተደርጎ እንደነበረና ያም ምርምርና ጥናት 5 ዓመት መዝለቁን ፤ ያሁን እንቅሥቃሴም የዚያ ተከታይ ፕሮጀክት መሆኑን ነው ፕሮፌሰር ገዛኸን ያስረዱን።
በታላቁ የምሥራቅ አፍሪቃ ስምጥ ሸለቆ ፣ እሳተ ገሞራ በያይነቱ ከፍተኛ እንቅሥቃሴ የሚያሳይበት፣ ለተመራማሪዎችም ፍንጭ የሚሰጥበት አካባቢ ወይም አካባቢዎች ቢኖሩ፤ የአፋር ኮረብቶችና የሠመጡ ደረቅ የየብስ ክፍሎች ናቸው። ለምሳሌም ያህል ከባህር ልክ በታች 120 ሜትር ገደማ የሆነውን ጨው፤ ድኝና ፖታሲየም ማዕድናት የሚገኙበትን ፤ ዳሉልን መጥቀስ ይቻላል።
ከእሳተ ገሞራ የሚገኝ እንፋሎት አንዱ የታዳሽ ኃይል ምንጭ መሆኑ የታወቀ ነው። በአነስተኛ ደረጃ የተሞከረ ቢሆንም ባለፈው ጸደይ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር 2 ቢሊዮን ዶላር የሚያስወጣ ፕሮጀክት ለማቋቋም የተስማማውን የአይስላንድ ኩባንያ መጥቀስ ይቻል ይሆናል።
ተክሌ የኋላ
አርያም ተክሌ