1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈፃፀምን ተከትሎ የሰብዓዊ መብት ሁኔታ አሽቆልቁሏል»

ዓርብ፣ ኅዳር 16 2009

የአፍሪቃ ኅብረት አካል የሆነዉ የአፍሪቃ የሰብዓዊና የሕዝቦች መብት ኮሚሽን ከትላንትና ወድያ ባወጣዉ የዉሳኔ መግለጫ በአሁኑ ግዜ በኢትዮጵያ ዉስጥ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈፃፀምን ተከትሎ የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እየከፋ መሄዱ በጣም እንዳሳሰበዉ ገልፀዋል።

https://p.dw.com/p/2TGsV
African Union Hauptquartier in Addis Abeba
ምስል AFP/Getty Images/J. Vaughan

MMT_African HR Comm. Resol. on Ethiopia - MP3-Stereo

መቀመጫዉን  ባንጁል፣ጋምብያ፣ ያደረገዉ ይህ ኮሚሽን በያዘዉ ዉሳኔ ላይ የኢትዮጵያ መንግሥት የሰዎች የመንቀሳቀስ፣ የመደራጀት መብት ፣ እንዲሁም በሚድያና በኢንተርኔት ላይ የጣለዉን እገዳ እንድያነሳም አሳስብዋል። በተጨማርም የታሳሪዎችን መብት በሕግ እንድያስጠብቅ፣ ያልተመጣጠነ ኃይል እንዳይጠቀምና ገለልተኛ አጣሪ ቡድን ተመስርቶ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዲመረምሩ ማድረግ እንዳለበት በዉሳኔዉ አስታዉቋል።

በጥቅምት ወር አጋማሽ ላይ በባንጁል ለሦስት ቀን የአፍርቃ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ባካሄዱት ስብሰባ በአገሪቱ አሉ የሚባሉ ችግሮች ተመርጠዉ ኮሚሽኑ አቋም እንድይዝ ግፊት ከተደረገበት ዉስጥ አንዱ አሁን በኢትዮጵያ ያለዉ የሰባዊ መብት ሁኔታ መሆኑን በስብሰባዉ የተሳተፉትና የስብስብ ለሰባዊ መብቶች ጉባኤ በኢትዮጵያ የሚመሩት አቶ ያሬድ ኃይለማርያም ለዶይቼ ቬሌ ይናገራሉ። ኮሚሺኑን ያዋቀሩት የመንግስታቶች ስብስብ በመሆኑ ከነሱ የፖለቲካ ተፅኖ ነፃ ልሆን ባይችልም «ጠንከር ያለ አቋም» መያዝ ችለዋል ሲሉ ይናገራሉ።

Addis Ababa (Äthiopien)
ምስል picture alliance/landov

የኢትዮጵያ መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ሲደነግግ የሰብዓዊ መብት «በምንም ዓይነት መልኩ መጣስ እንደሌሌበት አስረግጦ» አስቀምጠዋል የሚሉት በመንግስት ኮሙኒኬሼን የሕዝብ ግኑኝነት ሃላፊ አቶ መሃመድ ሳይድ ናቸዉ። የኢትዮጵያ መንግስት «ለዜጎቹ የሚሰማ ሃላፊነት » አለዉ የሚሉት አቶ መሃመድ፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተቋቋመዉ አጣሪ ቦርድ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን እየተከታተለ ነዉ ይላሉ።

ኮሚሽኑ እስረኞች ተገቢዉን የሕግ ከለላ እንዲያገኙና መንግስት ያልተመጣጠነ ኃይል እንዳይጠቀም ያሳስባል።

አሁን በኢትዮጵያ ያለዉ ወቅታዊ ሁኔታ «እጅግ አሳሳቢ» መሆኑንና በርካታ ሰዎች ከሕግ አግባብ ዉጭ ኢየተሳሩ መገኘታቸዉን ኮሚሽኑ ማሳሰቡን አቶ ያሬድ ይናገራሉ።

በፌስቡክ ድረ-ገፃችን ላይ የኮሚሺኑን የዉሳኔ መግለጫ እንዴት ይመለከቱታል ብለን አስተያየት ጠይቀነ ነበር። «በጣም ይገርማል፣ የአፍሪቃ ኅብረት ዉሳኔውን ከየት አመጣው በቃላትም ቢሆን ይሄ ራሱ አንድ ትልቅ ለውጥ ነው፣» ያሉን አሉ። ሌሎች ደግሞ «የታሳሩትን ከመሞት አያድንም፣ ያልታሰርንውን እንዳንሞት መፍትሄ አምጡ፣» የሚሉ ይገኙበታል።

 
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ