የርዮው የአካባቢ ጥበቃ ጉባኤ
ዓርብ፣ ሰኔ 15 2004የአፍሪቃ ክፍለ ዓለም በአየር ንብረት ለውጥ ከባድ ጉዳት ደርሶበታል ። ረሃብና የአየር ለውጥ ፣ በአሁኑ ሰዓት ክፉኛ የተጎዳውን የብዙ የአፍሪቃ ሃገራት ኤኮኖሚ ወደ ባሰ አዘቅት ሊያወርደው ይችላል ። ይህን መሰሉ ችግር ያጋጠማት አፍሪቃ ግን ለዓለም ሙቀት መጨመር አብይ ምክንያት በሆነው በከባቢ አየር ብክለት አትታማም ። ይህ ደግሞ የዶቼቬለው ኖኤል ኮኩ ታዴኞን እንደዘገበው የአፍሪቃ መንግሥታት ሪዮ ደጀኔሮ ብራዚል በተከፈተው ዓለም ዓቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ጉባኤ እንዲደመጡ በቂ ምክንያት ይሆናል ።
የአፍሪቃ መንግሥታት በርዮ ደጀኔሮ ው የአካባቢ ጥበቃ ጉባኤ አንድ አሳሪ ውል ላይ እዲደረስ ይፈልጋሉ ። ለዚህ ዓላማም የዲሞክራሲያዊት ሪፕብሊክ ኮንጎን ፕሬዝዳንት ዴኒስ ሳሶ ንጉዌሶን ቃል አቀባያቸው አድርገው መርጠዋል ። ፕሬዝዳንቱ በተለይ የተባበሩት መንግሥታት የአካባቢ ጥበቃ መርሃ ግብር በእንግሊዘኛው ምህፃር UNEP አቅም አድጎ ወደ ሙሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አካልነት እንዲለውጥ ማረጋገጥ አንዱ ፍላጎታቸው ነው ።
ኬንያ መዲና ናይሮቢ የሚገኘው UNEP መቀመጫውን በታዳጊ ሃገር ያደረገ ብቸኛውና ትልቁ የተባበሩት መንግሥታት መሥሪያ ቤት ነው ። ባለፈው ግንቦት መጨረሻ ላይ የአፍሪቃ መሪዎች ባካሄዱት ጉባኤ አሁን ባሉበት ሁኔታ ለዓለም ከጥቅማቸው ጉዳታቸው ያመዝናል የተባሉትን የነሃስ ወይም ከስል ድንጋይ ማእድናት ከማውጣት ይልቅ ለደን ለግጦሽ መሬትና ለባህር ጠረፎችም የላቀ ትኩረት ለመስጠት ነው የተስማሙት ። እነዚህን ማዕድናት የመውጣቱ ተግባር ለም ማሳዎችን ከጥቅም ውጭ ያደርጋል ። በርካታ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የአፍሪቃ ሃገራት ከርዮው ስብሰባ የተጨበጠ ውጤት ያገኛሉ ብለው አያምኑም ። እነርሱም ርዮ በመካሄድ ላይ ያለውን የአካባቢ ጥበቃ ጉባኤ የሚቃወም ህዝባዊ ያሉትን ሌላ ጉባኤ እዚያው ያካሂዳሉ ። ከተካፋዮቹ አንዱ የቤኒን ገበሬዎች ማህበር ዋና ፀሃፊ ናቸው ።
«ጨዋታው አብቅቷል ። መራህያነ መንግሥቱ እዚህ የመጡት ያለቀለት ና የተሰናዳ ውል ለመፈረም ነው ። ለኛ ለሲቪል ማህበራት ተወካዮች ይሄ እንዲታወቅ ማድረጉ ጠቃሚ ነው ። በጉዳዩ ላይ በበቂ ሁኔታ በሰፊው ተነጋግረናል ። ድሆችም እንደ ሃብታሞቹ ሁሉ እኩል መብት አላቸው ። የገጠር ነዋሪዎች የሚሰራበትን ፖለቲካ እንዲቃወሙ የሥልጣን ባለቤቶች በመሆን አቋማቸውን ተፈፃሚ እንዲያደርጉ ማደፋፈር አለብን ። ሙሳ ጎይታ በአፍሪቃ በግብርና የተሰማሩ አምራቾች ማህበር የመንግሥት ተወካዮች በርዮው ጉባኤ የአካባቢ ጥበቃ ተሟጋቾች ለሚሉት ደንታም ይኖራቸዋል ብለው አያስቡም ።
« የሚሰሙን አይመስለኝም ። ሆኖም እዚህ ቢያንስ ከፖለቲከኞች ጋር ለመነጋገር እድሉ አለ ። ለምሳሌ እኔ ከአንዳንድ ባለሥልጣናት ጋር እገናኛለሁና ምናልባትም በሚያደርጉት ድርድር ለማህበሩ የሚበጅ አቋም እንዲይዙ ማግባባት እችል ይሆናል ። እንዲያም ያም ብዙዎቹ እንደሚያምኑት ይህ የመሪዎች ጉባኤ መከሸፉ እንደማይቀር ነው የማስበው ። እዚህ ንግግር የሚያሰሙት ፣ የታመመችውን ፕላኔታችንን ለማስታመም ትንሽ ገንዘብ
እንደሚያከፋፍሉ የሚናገሩትና አረንጓዴ ኢኮኖሚ እያሉ ስም የሚሰጡት ወገኖች ራሳቸው የተፈጥሮ አካባቢን የሚበክሉ በተፈጥሮም ላይ ጥፋት የሚያደርሱት ናቸው ። »
በዚህ የተነሳም አፍሪቃ ለአካባቢ ጥበቃ ችግሮችዋ የራስዋን መፍትሄ መፈለግ ይኖርባታል ። ይህም በ 3ተኛው ዓለም የአካባቢ ጥበቃ ና የልማት እንቅስቃሴ በእንግሊዘኛው ምህፃር Enda ከተባለው ድርጅት የመጡት ሻይሽ ቲድያኔ ዴዬ አፅንኦት የሰጡት ጉዳይ ነው ።
« በመልማት ላይ ባሉ ሃገራት የሆነ ለውጥ ማምጣት ከተፈለገ ሃገራቱ የራሳቸውን ሃብት ከቴክኖሎጂ ጋር እንዲጠቀሙበት ማብቃት ነው ። ይህንንም ሲያደርጉ ከሰሜኑ ንፍቀ ክበብ እርዳታ ከመጠበቅ ይልቅ የራሳቸውን ኑሮ በራሳቸው ቢያሻሽሉ ይበጃቸዋል ። »
እሉታዊ ሁኔታዎች ቢኖሩም ሻይሽ ቲድያኔ ዴዬ የአፍሪቃ ድምፅ በርዮ ደጀኔሮው ጉባኤ ሳይሰማ አይታለፍም የሚል ተስፋ አላቸው ። »
ኖኤል ታዴኞን
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ