1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የራዶቫን ካራቺች ችሎት

ማክሰኞ፣ የካቲት 23 2002

የቦዝንያ ሰርቢያውያን እአአ ከ 1992 እስከ 1995 በቦዝንያ ሄርሶጎቪና በተካሄደው ጦርነት ወቅት ራሳቸውን ከሙስሊም መሰረተኞች ጥቃት ብቻ መከላከላቸውን የቀድሞ የቦዝንያ ሰርቢያውያን መሪ ራዶቫን ካራዲች አስታወቁ።

https://p.dw.com/p/MHtn
ምስል AP

ካራዲች ይህንን የገለጹት ዴን ኻግ ኔዘርላንድስ በሚገኘው የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት ለተመሰረተባቸው ክስ ትናንት የመከላከያውን ንግግር ባሰሙበት ጊዜ ነበር። ሰርቢያውያኑ በመንግስት የተደገፈ ሽብርተኝነት ሰለባ እንደነበሩ የስድሳ አራት ዓመቱ ካራዲች ዛሬም በቀጠለው ችሎት ላይ አክለው አስረድተዋል። ፍርድ ቤቱ ካራዲችን በቦዝንያ ጦርነት ወቅት በስብዕና አንጻር በተፈጸሙ የጦር ወንጀሎች ክስ መስርቶባቸዋል።

ለቦዝንያ ጦርነት ሙስሊሞችና ብዙ ምዕራባውያን ፖለቲከኞች፡ ከነዚህም መካከል በተለይ አሜሪካውያን፡ ጀርመናውያን እና ብሪታንያውያን ጭምር ጥፋተኞች ናቸው። ይህ አነጋገር የቀድሞው የየቦዝንያ ሰርቢያውያን መሪ ራዶቫን ካራቺች ትናንት በዴን ኻግ ኔዘርላንድስ በርሳቸው ላይ የተመሰረተውን ክስ የሚመለከተው ችሎት በተጀመረበት ጊዜ ራሳቸውን ለመከላከል ያሰሙት የንግግር ዋነኛው መልዕክት ነበር። ካራቺች የቦዝንያ ሙስሊሞችን ከሀገራቸው ለማባረር ፈልገው እንደማይውቁ ገልጸዋል፤ ይሁን እንጂ፡ የቦዝንያ ሙስሊሞች የቀድሞዋን ዩጎዝላቭያ ስልጣን በጠቅላላ ለመያዝ በፈለጉበበት ጊዜ ካራዲች ይህንን ማስወገዱን እንደ ቅዱስ ተግባራቸው ተመልክተውታል። ዓላማቸውንም በአስተርጓሚያቸው አማካኝነት እንደሚከተለው አስረድተዋል።

"ሀገራቸውን ፡ ህዝባቸውን እና ንብረቱን ብቻ ለመከላከል ነበር የፈለጉት።"

Karadzic vor Gericht
ምስል AP

በጦር ወንጀል እና በስብዕና አንጻር በተፈጸሙ በርካታ ወንጀሎች የተከሰሱት የቀድሞው የቦዝንያ ሰርቢያውያን መሪ ራዶቫን ካራዲች በዚሁ አነጋገራቸው እአአ በዘጠናቻዎቹ ዓመታት መጀመሪያ ላይ ስለተካሄደው የቦዝንያ ጦርነት ያላቸውን አስተያየት ለመጀመሪኢያ ጊዜ በይፋ አስታውቀዋል። የተም የመደበላቸውን ጠበቃ ያልተቀበሉት እና በንቀት የተመለከቱት ካራዲች በችሎቱ ላይ አሁንም ራሳቸውን የመከላከሉን ተግባር ቀትለውበታል። በትናንቱ ዕለት ሁለት ረዳት የህግ ባለሙያዎች ይዘው በፍርድ ቤቱ ቢቀርቡም፡ የመክፈቻውን ንግግር ብቻቸውን ነበር ያሰሙት። ቀንደኛ የጎሳ ጭፍጨፋ አራማጅ የተባሉት ካራዲች ዘጠና ደቂቃ ሙሉ ሳያቋርጡ ፈጥነው እና አንዳንዴም በእጆቻቸው በመደገፍ ባቀረቡት ንግግራቸው ላይ በቦዝንያ ጦርነት ላይ ስለተጫወቱት ሚና አስረድተዋል።

"ኃላፊነቱን አስተናንሼ ለማቅረብ አልፈልግም። ከፍተኛ ስልጣን ነበረኝ እና ኃላፊነቱን ወደሌሎች ለመግፋት ባለመፈለጌ ለራሴ ጥብቅና ቆሜአለሁ።"

ካራዲች በሰርብኛ ቋንቋ እንዳስረዱት፡ በተመሰረተባቸው ክስ ላይ ለራሳችው ጥብቅና የቆሙበት ድርጊት ለራሳቸው ጥቅም ብቻ አይደለም።

"ለራሴ ብቻ ሳይሆን፡ ለሀገሬ እና ለህዝቤ ጥብቅና መቆም እፈልጋለሁ። ይህ ለኔ በርግጥ ቅዱስ ተግባር ነው፤ ራሴን እና ሀገሬን የመከላከል አቅሙም አለኝ።"

ራዶቯን ካራዲች በአንጻራቸው በተመሰረተው ክስ ላይ የቦዝንያ ሙስሊሞች መረጃ ማጭበርበራቸውን ለማሳመን በማሰብ፡ ልክ ካሁን ቀደም ዓቃቤ ህግ ክሱን በመሰረተበት ንግግሩ እንዳደረገው ሁሉ ፡ እርሳቸውም የቪድዮ ደጋፊ ማስረጃዎችን አቅርበዋል። በጭነት ተሽከርካሪዎች ላይ የአስከሬኖች ክምር የታየበት ዘግናኝ ስዕል ችሎቱ በተካሄደበት የተመድ የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት ክፍል ውስጥ ታይቶዋል። ካራዲች ስለተከሰሱበት አስከፊ የጭካኔ ተግባር፡ ስምንት ሺህ የቦዝንያ ሙስሊሞች ስለተገደሉበት የስሬብሬኒሳ ጭፍጨፋ ጭምር ዛሬም አስተያየት አልሰጡም።

ዩርገን ክላይካምፕ/አርያም ተክሌ

ተክሌ የኋላ