የማሊ ዉጊያ: ታሪካዊ ቅርሶቿና ሠልፍ
ሐሙስ፣ ሰኔ 28 2004
የማሊ ሙስሊም አማፂያን በታሪካዊቷ የቲምቡክቱ ከተማ የሚገኙ ጥንታዊ ቅርሶች ማፈራረሳቸዉን ዓለም አቀፉ ማሕበረሠብ እያወገዘ ነዉ።ቅሮሶቹን የሚያፈራርሰዉ አንሳር ዲን የተሰኘዉ አማፂ ቡድን ግን ሰሜናዊ ማሊን ከተቆጣጠረ ወራት አልፈዉታል።ሲሆን መላዋ ማሊን ካልሆነም የሚቆጣጠረዉን አካባቢ በሸሪዓ ሕግ ለመግዛት የሚፋለመዉ ቡድን አላማዉን የሚቃወሙ በርካታ ሠላማዊ ሰዎችን መግደሉም ተዘግቧል።ትናንት ርዕሠ-ከተማ ባማኮ ዉስጥ ቡድኑን በመቃወም አደባባይ የወጣዉ የከተማዊቱ ነዋሪ አማፂያኑን በጠመጃ ለመፋለም መቁረጡን አስታዉቋል።ፔተር ሒለና ያሕያ ኮናቴ የዘገቡትን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።
ባማኮ-ትናንት።ዝናብ ይወርዳባትል፥ ንፋስ ያፏጭባታል።ዉሽንፍር ይላተምባታል።የነፃነት አደባባይዋን ደግሞ እነሱ ሙጥኝ ብለዉበታል።ሁለት ሺሕ ይገማታሉ።ብዙዎቹ የሰሜን ማሊ ተወላጆች ናቸዉ። ከዝናብ-ዉሽንፍሩ በላይ የሚያሳስብ-የሚያሰጋ፥ ምናልባትም የሚጎዳ ችግራቸዉ ያደረጉትን እንዲያደርጉ ሳያስገድዳቸዉ አልቀረም።ንፋስ፥ ዉሽንፍሩን ከመቋቋም በላይ ለማድረግ ይፈክራሉም።
«ጠመንጃ እንፈልጋለን» ሰሜኑን ነፃ ለማዉጣት፥ ትጥቅ እንፈልጋለን።ሰሜኑን ነፃ ለማዉጣት።»
ሰልፈኞቹ አስታጥቁን የሚሉት ሰሜናዊ ማሊን በቅርቡ «ነፃ አወጣን» ካሉት ከአንሳር ዲን አማፂያን እጅ ለማስለቀቅ ነዉ።የሐገሪቱ ጦር ሐይል ግን ሠልፈኞቹን ከበፊትም ጀምሮ አያምናቸዉም። ኦስማን ኢሱፍ ማይጋ የማሊ የምክር ቤት እንደራሴ ነበሩ።አሁን ደግሞ COREN በሚል የፈረንሳይኛ ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ የየሰሜናዊ ማሊ ሕዝብ ማሕበር መሪ ናቸዉ።የሰሜናዊ ማሊ ሁኔታ ጊዚ አይሰጥም ይላሉ።
«ሁኔታዉ ለሕዝቡ (ለሰሜን ማሊ) ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከበደ፥ እየባሰ፥ አስከፊ እየሆነም ነዉ። ምክንያቱም እዚያ መጥፎ የሚለዉ ቃል ሊገልፀዉ የሚችለዉ መጥፎ ሁሉ እየተፈፀመ ነዉ።ለዚሕ ነዉ እዚሕ ታሪካዊ ሥፍራ (ነፃነት አደባባይ) ተሰብስበን ሥጋታችንን ለመግለፅ የወሰነዉ።እና ሐገራችንን መልሰን ለመቆጣጠር መላዉን ማሊ ለማንቀሳቀስ የፈለግነዉ።»
የአንሳር ዲን ተዋጊዎች ታሪካዊ ቅርሶችን ማፍረሳቸዉ ከተሰማ ወዲሕ የዉጪ ሐይል ወደ ማሊ ይዝመት የሚለዉ ሐሳብ ደገምገም-ደመቅ እያለ ነዉ።እንደሚወራዉ ማሊ አባል የሆነችበት የምዕራብ አፍሪቃ የምጣኔ ሐብት ማሕበረሰብ በእንግሊዝኛ ምሕፃረ ቃሉ (ECOWAS) 3300 ወታደሮች ወደ ማሊ ለማዝመት በተጠንቀቅ አቁሟል።
የፈረንሳዩ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሎራ ፋቢዩስ በበኩላቸዉ በማሊ ጉዳይ የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት እንዲወስን ጠይቀዋል።ቲምቡክቱ ከአማፂያኑ እጅ ከመዉደቋ በፊት ለምክር ቤት አባልነት የተመረጡባት ሳንዲይ ማሐማነ እንደሚሉት ደግሞ ወታደራዊ እርምጃ አስፈላጊ ብቻ አይደለም። አስቸኳይ ጭምር እንጂ።
«የጦር ሐይል እርምጃ በጣም አስፈላጊ ነዉ።ሁሉቱም፥ የማሊ ጦርም የዉጪ ሐይልም ባስቸኳይ እርምጃ መዉሰድ አማራጭ የሌለዉ ጉዳይ ነዉ።»
የማሊ ጦር ሐይል የሐገሪቱን ፕሬዝዳት ከሥልጣን ካስወገደ ወዲሕ ምዕራብ አፍሪቃዊቱ ሐገር በሕዝብ የተመረጠ ቋሚ መንግሥት የላትም።የማሊን ፖለቲካዊ ቀዉስ ለማስወገድ የሚጥረዉ ኤኮዋስ ባማኮ ላይ ብሔራዊ የአንድነት መንግሥት ካልተመሠረተ የቱዋአሬጎችን ይሑን የሙስሊም ፅንፈኞችን አመፅ ማስወገድ፥ ሐገራቱንም ማረጋጋት አይችልም ባይ ነዉ።
ለትናንቱ ሠልፈኞች ግን ጊዜዉ እየከነፈ ነዉ።ፈጣን እርምጃ እንዲወሰድ ይፈልጋሉ።አለበለዚያ ብዙዎቹ ከትዉልድ ቀየ፥ ከተማቸዉ እንደተፈናቀሉ ቀሪ ሕወታቸዉ ለመግፋት ይገደዳሉ።
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሰ