የማሊ ተልዕኮ እና አጠያያቂው የቻድ ተሳትፎ
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 27 2005
የዚሁ ጦር ተልዕኮ አወቃቀርን የተመለከተው ጥያቄ፡ በተለይ ጠንካራ ጦር ያላት፡ ግን በሰብዓዊ መብት ይዞታዋ የምትወቀሰዋ ቻድ በተልዕኮው ትልቅ ሚና እንድትይዝ የቀረበው ሀሳብ በምክክሩ ወቅት ጠንካራ ክርክር አስነስቶዋል። ቻድ በማሊ ሊደረግ በታሰበው የጦር ተልዕኮ ትሳተፍ መባሉን የመብት ተሟጋቾች በእሣት እንደመጫወት ተመልክተውታል።
በረኃማ እና አልፎ አልፎ የግራር ዛፎች ብቻ የሚታዩበት የሳር መሬት የያዘው ሰሜናዊው የማሊ አካባቢ እጅግ አዳጋች መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ እንዳለው ይነገራል። በንዲህ ዓይነቱ በረኃማ አካባቢ ውጊያ የማካሄድ ልምድ ያለው ወታደር ብቻ ነው ዕድል ያለው። በተመሳሳይ አካባቢ የሚኖሩት የቻድ ጦር ኃይላትም ይህ ተሞክሮ አላቸው። በመሆኑም ቻድ በማሊው ተልዕኮ የምትሳተፍበት ውሳኔ ገሀድ የሚሆንበት አዝማሚያ እየተቃረበ ነው። በማሊው ተልዕኮ ላይ ቻድ ትሳተፍ የሚለውን ሀሳብ በተለይ በጣም የገፋችበት ከዚችው ሀገር ጋ የጠበቀ ግንኙነት ያላት የቀድሞዋ ቅኝ ገዢ ፈረንሣይ ስትሆን፡ ለቻድ ጦር መጠናከር በምትሰጠው የጦር መሣሪያ ርዳታ ድርሻ አበርክታለች። የፈረንሣይ ፕሬዚደንት ፍራንስዋ ኦሎንድ የቀድሞዎቹ የሀገራቸው መንግሥታት አፍሪቃውያን ርዕሳነ ብሔርና መራሕያነ መንግሥትን የሚያባብሉበት ፖሊሲ እንዳከተመለት ቢገልጹም፡ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በቅርቡ በማሊ ይጀመር ለሚባለው የጦር ተልዕኮ በቻድ ርዳታ ላይ ጥገኛ መሆኑን ተገዶዋል።
ይህ ዓይነቱ አጋርነት ግን አጠያያቂ ነው። እርግጥ፡ ቀውስ ባዳቀቀው የሳህል አካባቢ ቻድ መረጋጋት የሚታይባት ሀገር ናት። ይሁንና፡ ለዚህ መረጋጋት ምክንያት የሆነው ቻድን ካለፉት ሀያ ዓመታት ወዲህ በሥልጣን ላይ የሚገኙት ፕሬዚደንት ኢድሪስ ዴቢ የሚከተሉት አርቆ የመግዛት ፖሊሲ ነው። የተቃዋሚ ወገኖችን ይጨቁናሉ፤ ሀሳብ በነፃ የመግለጽን ነፃነት ያፍናሉ። በሀገሪቱ መንግሥት ውስጥ ስለሚታየው ሙስና በአምዱ አንድ ዘገባ ያወጣ አንድ ሣምንታዊ መጽሔት ለምሳሌ ባለፈው መስከረም ወር የመዘጋት ዕጣ ሲገጥመው፡ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ እና ዘገባውን ያዘጋጁት የሙያ ማህበራት አባላት ታስረዋል። አንድ የተቃዋሚ ቡድን ፖለቲከኛም በሕገ ወጥ አደን ተሳትፈሀል በሚል ሰበብ እንዲሁ የመታሰር ዕጣ ገጥሟቸዋል። በቻድ የሚፈፀመው የሰብዓዊ መብት ረገጣ ተዘርዝሮ እንደማያበቃ የዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት፡ የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ባልደረባ ክሪስቲያን ሙኮሳ ገልጸዋል።
« አንድ ጳጳስ በስብከት ወቅት ሀገሪቱ ከነዳጅ ዘይት የምታገኘው ገቢ በቻድ ሕዝብ መካከል በትክክል አልተከፋፈለም ብለው በመናገራቸው ብቻ በዚህ በጥቅምት ወር ሀገሪቱን ለቀው እንዲወጡ ተገደዋል። አንድ ጳጳስ ሀገር ለቆ እንዲወጣ ሲደረግ ይህ የመጀመሪያ ጊዜ ነው። »
የመንግሥቱ የጭቆና ተግባር በማስፈራራት ላይ ብቻ ተወስኖ እንዳልቀረ ነው ሙኮሳ አክለው ያስረዱት።
« ጋዜጠኞችን ለማስፈራራት እና ለማጉላላት፡ እንዲሁም፡ የሀያስያን ድምፅን ለማፈን እየተባለ እነዚህን ወገኖች ለፍርድ የማቅረቡ አሰራር አዲስ ነው። ቀድሞ የማስፈራራቱ ተግባር በግልፅ አልነበረም የሚካሄደው። የሀገሪቱ መንግሥት አሁን የፍትሁን አውታር ተቃዋሚዎቹን ሆን ብሎ ለማስፈራሪያና ለመጨቆኛ የሚጠቀምበት አዲስ ዘዴ ነው። »
ይህ እየታወቀ ሳለ አሁን የቻድን ወታደሮች፡ በሚገባ የታጠቁ በመሆናቸውና በበረኃ ውጊያ ልምድ ስላላቸው ብቻ ፡ በማሊው የጦር ተልዕኮ ለማሳተፍ መታሰቡ የምዕራቡን ዓለም ተዓማኒነት አጠያያቂ እንደሚያደርገው በፍራይቡርግ የሚገኘው የአርኖልድ ቤርግሽትሬሰር ተቋም የፖለቲካ ተንታኝ ጀርመናዊትዋ ሄልገ ዲኮቭ አጠያይቀዋል።
« የጦር ኃይል ስላስፈለገን ብቻ፡ ሥርዓተ ዴሞክራሲ እንዲተከል የምንጠይቀው እኛ ምዕራባውያን፡ ቻድን የመሰለችን ሀገር መደገፋችን ምን ዓይነት መልዕክት ያስተላልፋል? »
እንደ ሄልገ ዲኾቭ አስተያየት፡ የማሊው የጦር ተልዕኮ ለቻድ ፕሬዚደንት ኢድሪስ ዴቢ ዓለም አቀፍ እውቅና ይሰጣል። ምክንያቱም ዴቢ፡ ምንም እንኳን ይኸው ቅድመ ግዴታ እስካሁን በግልጽ ባይታወቅም፡ የሀገራቸው ጦር በማሊው ተልዕኮ ይሳተፍ ዘንድ የሚያቀርቡት ቅድመ ግዴታ ሥልጣናቸውን ለማጠናከር የሚረዳቸው እንደሚሆን አያጠራጥርም። ከዚህ ሌላ የሙሥሊም ፅንፈኝነት በዚችው የማዕከላይ አፍሪቃ ሀገርም ላይ ስጋት ደቅኖዋል። የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት፡ ሰሜናዊው የቻድ አካባቢም ልክ እንደ ማሊ የሙሥሊም ተፅዕኖ የበዛበት ሲሆን፡ የዚሁ አካባቢ ነዋሪዎች ሰሜናዊ ማሊን የተቆጣጠሩትን የአክራሪ ሙሥሊሞች የአንሳር ዲን ቡድንን እንደሚደግፉ ተጨባጭ ማስረጃዎች መገኘታቸውን ነው ሄልገ ዲኮቭ የገለጹት።
« በቻድ መዲና ንጃሜናም አክራሪ ሙሥሊሞች አሉ። አሁን ግልጽ አይታዩም። ማን መሆናቸውም አይታወቅም። ናይጀሪያ ካለው የሙሥሊም አክራሪዎች ቡድን ከቦኮ ሀራም ጋ የቅርብ ግንኙነት አላቸው። ቻድ ወታደሮችዋን ወደ ማሊ ከላከች ቦኮ ሀራም የቻድን መረጋጋት እንደሚያደፈርስ በሀገሪቱ ባለ አንድ የሙሥሊም አክራሪዎች ክበብ አማካኝነት በፕሬዚደንት ኢድሪስ ዴቢ ላይ ዛቻ ሰንዝሮዋል። »
በነገራችን ላይ ከቻድ ጎን፡ ሌላዋ ያካባቢው ሀገር አልጀሪያ በበረኃማ አካባቢ የውጊያ ልምድ ማካበትዋ ይነገራል። ይሁንና፡ ሰሞኑን ከዩኤስ አሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሂለሪ ክሊንተን ጋ በማሊ ጉዳይ ላይ በመዲናይቱ አልዥየ የተወያዩት የአልጀሪያ ፕሬዚደንት አብደልአዚዝ ቡቴፍሊካ ሀገራቸው በማሊው ተልዕኮ ላይ የመሳተፍ ዕቅድ እንደሌላት ነው ነው ያጎሉት። ይኸው የአልጀሪያ መልስ የቻድ ጦር በማሊው ተልዕኮ የሚሳተፍበትን ድርጊት አስፈላጊነት እያጠናከረው ተገኝቶዋል።
ቬራ ኬርን/አርያም ተክሌ
መሥፍን መኮንን