የሙጋቤ ሰባተኛ የሥልጣን ዘመን አንደኛ ዓመት
ሐሙስ፣ ሐምሌ 24 2006ሙጋቤና አሁንም ያልተቀየረው አቋማቸው የቀጣዩ ዘገባ ትኩረት ነው ። የዚምባብዌ ገበሬዎች ማህበር እንደሚለው በአሁኑ ጊዜ በሃገሪቱ የመሬት ባለቤት የሆኑ ነጮች ቁጥር ወደ 150 ይጠጋል ። ቀደም ሲል በተለይ በ2000 ዓም መጀመሪያ ላይ ወደ አራት ሺህ የሚጠጉ ነጮች በሙጋቤ ትዕዛዝ መሬታቸው ተወስዶባቸዋል ። ሙጋቤ ያሉት በተግባር የሚተረጉም ከሆነ የቀሩት ነጭ ገበሪዎች መሪታቸውን ጥለው መውጣት ይኖርባቸዋል ። ለሰባተኛ የሥልጣን ዘመን ሃገሪቱን በመምራት ላይ ያሉት የ90 ዓመቱፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤና ፓርቲያቸው ዛኑ ፒኤፍ ባለፈው ዓመቱ ምርጫ በአብላጫ ድምፅ አሸንፈው ካለፈው ዓመት አንስቶ ሃገሪቱን ካለተቀናቃኛቸው ሞርጋን ስቫንጊራይ ለብቻቸው መምራት ቢችሉም ያከናወኑት ግን እዚህ ግባ አይባልም ይላሉ በዚምባብዌ የኮናርድ አደናወር ተቋም ሃላፊ ዩርገን ላንገን ። በርሳቸው አባባል በዚህ አንድ ዓመት ውስጥ የብድር ቀውስ የኤኮኖሚ እድገትም ይሁን ሌሎች የአመራር ደንቦችን የተመለከቱ ጉዳዮች ቢሆኑ ባሉበት እንደቆሙ ናቸው ።
«ባለፉት 12 ወራት የሃገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ ምን ይመስል እንደነበረ በአንድ አረፍተ ነገር ብቻ መግለፅ ይቻላል ። ፀጥ እረጭ ያለ ነበር ።ሃገሪቱ ወደፊትም ሆነ ወደ ኃላ አትሄድም ባለችበት እየረገጠች ነው ። በዚህ አጋጣሚ አንድ ነገር ግልጽ ይሆናል ። የዛኑ ፒኤፍ አባላትም ሳይቀሩ በመንግሥታቸው ላይ ያላቸው እምነት ጠፍቷል ። በሃገር ውስጥም ቢሆን የተሳካ ፖሊሲ አለ የሚለው እምነት የተመናመነ ነው ።»
በአሁኑ ጊዜ ዚምባብዌ ብዙ ችግሮች አሉባት። ሃገሪቱ በ 2000ዎቹ ዓመታት ካጋጠማት የኤኮኖሚ ቀውስ ገና አላገገመችም ። በወቅቱ የዚምባብዌ የዋጋ ግሽበት ንሮ በመቶ ሚሊዮኖች ከመቶ ድረስ መጠጋቱ፣ ኮሌራ አራት ሺህ ሰዎችን መግደሉ እና ሃገሪቱ ከባድ የኤኮኖሚ ቀውስ ውስጥ መዘፈቋ በዓለም ዙሪያ ዐርዕስተ ዜና ነበር ። በመካከሉ የዋጋ ግሽበት ተስተካክሏል ። ሆኖም ኤኮኖሚው ያን ያህል እያደገ አይደለም ። እጎአ በ2013 እድገቱ 1.8 ከመቶ ነበር ። በሃራሬ ዩኒቨርስቲ የኤኮኖሚ ፕሮፌሰር ቶኒ ሃውኪንስ የግብርናው ምርት ጥሩ ባይሆን ኖሮ ሁኔታው ከዚህም የባሰ ይሆን ነበር ይላሉ ።አሁን ሃገሪቱ ያስመዘገበችው እድገት ስር የሰደደውን ድህነት ለመቀነስ በቂ አይደለም ። ያም ሆኖ ሮበርት ሙጋቤ አሁንም ዚምባብያውያንን የሃብት ባለቤት ለማድረግ በቀየሱት መርሃቸው እንደፀኑ ነው ። የሃገሪቱ ደንብ የውጭ ኩባንያዎች ከሚያፈሱት መዋእለ ንዋይ 51 በመቶው የሃገሬው ዜጎች ድርሻ እንዲሆን ያስገድዳል።
በተለይ ትላልቅ ማዕድን አውጭ ኩባንያዎች ይህ ህግ ያስከተለውን መዘዝ እየታገሉ ነው ። ኩባንያቸውን ሌላ አካል እንዲቆጣጠረው አሳልፈው ለመስጠት የሚስማሙ ጥቂቶች ናቸው ። ይህ ህግ ሃገሪቱ አሁን በአፋጣኝ የሚያስፈልጓትን የውጭ ባለወረቶች ተስፋ እያስቆረጠ ነው ። ይሁን እንጂ ሙጋቤ ይህን አቋማቸውን የማላላት ሃሳብ የላቸውም ።በዚምባብዌ የኮናርድ አደናወር ተቋም ሃላፊ ዩርገን ላንገን
«እንደሚመስለኝ ሃብትን በሃገሪው ቁጥጥር ስር የማድረጉ መርህ ይቀጥላል ። በአንድ ወቅት ወጣት የፓርላማ አባላት ጉዳዩን ለማለዘብና በጉዳዩም ላይ ለመነጋገር ያላቸውን ፍላጎት ለማሳየት ሞክረው ነበር ።ይሁንና በቀጥታ ታላቁ መሪ በግላቸው በተቻለ ፍጥነት ጉዳዩን አስቁመውታል። በተደነገገው 51 በመቶ ይፀናል ሲሉ ። እዚህ ላይ ምንም ዓይነት ለውጥ የሚደረግ አይመስለኝም ።»
በሙጋቤ እምነት ዚምባብዌ ነፃነትዋን ሙሉ በሙሉ የምትቀዳጀው አገሬው የራሱን ሃብት መቆጣጠር ሲችል ብቻ ነው ። ይሁንና ይህ መርሃቸው እስካሁን ምን ዓይነት ውጤት አለማምጣቱን ነው ኤኮኖሚስቱ ፕሮፌሰር ሃውኪንስ የሚናገሩት ።በዚህ ላይ ሃውኪንስ እንደሚሉት ርሳቸውን ማን ይተካል የሚለውም ሌላው አነጋጋሪ ጉዳይ ነው ።
« ማን ይተካል በሚለው ብዙ ትግል አለ ። ሙጋቤ 90 ዓመታቸው ነው ከአሁን በኋላ ብዙ ሊቀጥሉ አይችሉም ። ስለዚህ አንዳንድ ቦታዎችን ለመያዝ በርካታ እንቅስቃሴዎች አሉ ።አሁኑ የሙጋቤ ፓርቲ ኤኮኖሚውን መልሶ መገንባቱ ላይ ሳይሆን ማን ይተካቸዋል ማንስ ዋናውን ስራ ያገኛል ወደሚለው ላይ ያተኮረ ይመስላል ። »
ዳንኤል ፔልትስ
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ