1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሙአመር ኧል ጋዳፊ ቀብር እና የደጋፊዎቻቸው አስተያየት

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 14 2004

የቀድሞው የሊቢያ መሪ ሙአመር ኧል ጋዳፊ በሊቢያ በአንድ በምሥጢር በተያዘ ቦታ መቀበራቸው ተገለጸ። ጋዳፊ፡ ልጃቸው ሙዋታሲም እና የመከላከያ ሚንስትራቸው አቡ በከር ዩኒስ ጃበር ጥቂት ቤተዘመድ እና የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት ንጋት ላይ በእሥላማዊው ሀይማኖት ደንብ መሠረት ሥርዓተ ቀብራቸው መፈጸሙን የሽግግሩ ብሔራዊ ምክር ቤት አስታውቋል።

https://p.dw.com/p/RsuD
ምስል dapd
Mustafa Abdul Jalil Übergangsregierung Libyen
የሽግግሩ ምክር ቤት መሪ ሙስጠፋ አብደል ጃሊልምስል picture alliance/landov

ጋዳፊ ቢዘገይ በሀያ አራት ሰዓት ውስጥ መቀበር ሲገባቸው ይህን ያህል ጊዜ ሳይቀበሩ መቆየታቸው የእሥልምናን ደንብ ጥሰዋል። የሽግግሩ ብሔራዊ ምክር ቤት ጦር ኃይል ቃል አቀባይ ኢብራሂም ቤይት አል ማል የጋዳፊ እና አብረዋቸው የሞቱት ልጃቸው እና የመከላከያ ሚንስትራቸው ቀብር ዛሬ ሊነጋጋ ሲል መፈጸሙን አረጋግጠዋል።

«ቀብሩን የሚያስፈፅም አንድ ኮሚቴ ተቋቁሞዋል። ይኸው ኮሚቴ በፀጥታ ጥበቃ ምክንያት ሲባል ቀብሩን በአንድ ባልታወቀ ቦታ አስፈጽሞዋል። »

ከግብዓት መሬቱ በፊት ሦስት ሼኮች ለማቾቹ ፀሎት እንዳደረጉላቸው ቤይት አል ማል አክለው አስረድተዋል።

ምዕራቡ ዓለም የጋዳፊን ህልፈተ ሕይወት እንደ ትልቅ ድል ቢመለከተውም፡ ሞታቸው በተለይ የብዙ የአፍሪቃ ሀገሮች ሕዝቦችን ዘንድ አሳዝኖዋል። የሙአመር ኧል ጋዳፊ መንግሥት ባንዳንድ ማሊን በመሳሰሉ ድሆች አፍሪቃውያት ሀገሮች እስከ አንድ መቶ ሀምሣ ቢልየን የሚቆጠር ዶላር አፍስሶዋል። የዜና ምንጮች እንደሚሉት፣ ብዙ አፍሪቃውያን ግን በጋዳፊ ርዳታ ወደተሰሩ መስጊዶች በመሄድ ጸረ ኢምፔርያሊስት እና ለጋሽ የሚሉዋቸው ጋዳፊ በመሞታቸው የተሰማቸውን ሐዘን እየገለጹ ነው። በዩጋንዳ መዲና ካምፓላ ትምህርት ቤት፡ አሠላሣ ሺህ ሰው የሚይዝ መስጊድ፡ ከሞባይል ስልክ ኩባንያዎች እስከ ብስኩት ፋብሪካዎች አሰርተዋል። የሰሜን አትላንቲክ የጋራ መከላከያ ኪዳን ኔቶ የጋዳፊ ጦር በሲቭሉ ሕዝብ ላይ ወሰደው ያለውን የኃይል ርምጃ ለማብቃት ሲል በጋዳፊ አንፃር ያካሄደውን ያየር ጥቃት እአአ በ 2002 ዓም ምሥረታው ላይ ጋዳፊ የረዱት የአፍሪቃ ህብረት የአፍሪቃ ህብረት አውግዞታል። የኔቶን ጥቃት በጥብቅ የተቃወሙት የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት ጄኮብ ዙማ ጋዳፊ ተይዘው ለፍርድ መቅረብ እንጂ መገደል እንዳልነበረባቸው በቅሬታ ገልጸዋል። ጋዳፊን ከሥልጣን ለማውረድ ኔቶ የተጫወተውን ሚና በአህጉሩ ብዙ የጋዳፊ ደጋፊዎች እንደ ጣልቃ ገብነት እና እንደ አዲስ ቅኝ አገዛዝ ነው የተመለከቱት። በኮንጎ ብራዛቪል መምህርት የሆኑት የሀምሣ ሁለት ዓመትዋ ምቦሳ ነፃ የሆነች አፍሪቃን ማየት አይፈልጉም ያሉዋቸው ምዕራባውያን መንግሥታት አንድ ለሆነች ጠንካራ አፍሪቃ ምሥረታ የሚታገሉትን ሁሉ ለመግደል ወደ ኋላ ብለው አያውቁም በማለት ጋዳፊ በደጋፊዎቻቸ ዘንድ ሁሌ እንደ ሠማዕት እንደሚታዩ ገልጸዋል።

Süsafrika Jacob Zuma nach der Wahl
ፕሬዚደንት ጄኮብ ዙማምስል AP

ሀያስያን ጋዳፊ ባደረጉት ርዳታ በአፍሪቃ ብዙ ደጋፊ እንዳተረፉ ቢያስታውሱም፡ በአህጉሩ በጭካኔአቸው የሚፈሩ አንዳንድ ዓማፅያን መሪዎችን እና እጅግ የተጠሉትን የዩጋንዳ አምባገነን መሪ ኢዲ አሚንን የመሳሰሉ አምባገነኖችን በመርዳታቸው ብዙ ወቀሳ ተፈራርቆባቸው እንደነበርም ገልጸዋል። እንደሚታወሰው፡ ጋዳፊ በመጨረሻዎቹ የሥልጣን ዘመናቸው ለመርዳት ስድስት መቶ ወታደሮችን ወደ ዩጋንዳ ልከዋል፤ በቀድሞው የላይቤሪያ ፕሬዚደንት ቻርልስ ቴይለር ይረዱ የነበሩ ሕፃናትን በውትድርና ይመለምሉና ሰለባዎቻቸውንም እጅና እግር ይቆርጡ የነበሩትን የሲየራ ልዮን ዓማፅያንን በገንዘብ በረዱበት ድርጊት ላካባቢው አለመረጋጋት ድርሻ እንዳበረከቱ ነው የሚናገሩት።

Libyen Saif al Islam Gadhafi in Tripolis
ሰይፍ አል ኢዝላም ጋዳፊምስል dapd

ጋዳፊ በዛሬው ቀብራቸው የመጨረሻውን ዕረፍት ባገኙበት ባሁኑ ጊዜ ልጃቸው ሰይፍ አል ኢዝላም ሊቢያን፡ ኒዠርን እና አልጀሪያን በሚያዋስነው የሶስትዮሽ ማዕዘናዊ ድንበር ወዳለው የጋት አካባቢ መሸሻቸው ተገልጾዋል።

አርያም ተክሌ

ተክሌ የኋላ