1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመኢአድና የአንድነት ፓርቲዎች ሥምምነት

ረቡዕ፣ ሰኔ 4 2006

የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተቃዋሚ-ይባሉ ገዢ፤ ያገር ዉስጥ ይሁኑ የዉጪ ለመተባባር፤ ግንባር ለመፍጠር፤ ለመዋሐድ ሲዋዋሉ፤ መዋዋላቸዉ በተነገረ ማግሥት መለየያየት፤ መጣላት መወቃቀሳቸዉ ከመደጋገም አልፎ-ተለምዷል።ያለፈዉ ላለመደገሙ ለጊዜዉ ማረጋገጫ የለም። ካለም አቶ ስዩም «ተምረናል» ያሉት ነዉ።

https://p.dw.com/p/1CGlr

የመላዉ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና የኢትዮጵያ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ (አንድነት) ፓርቲዎች በእንድ ወር ጊዜ ዉስጥ እንድሚዋሐዱ አስታወቁ። የሁለቱ ፓርቲዎች ባለሥልጣናት ባለፈዉ ዕሁድ በተፈራረሙት ዉል መሠረት ፓርቲዎቹ በቅርቡ ተዋሕደዉ አንድ ፓርቲ ይመሠርታሉ። ፓርቲዎቹ ከሥምምነት የደረሱት ከረጅም ጊዜ ድርድርና ዉይይት በኋላ ነዉ። ሁለቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሥምነታቸዉ መሠረት የሚመሠርቱት የተዋሐደ ፓርቲ ትልቁ ብሔራዊ ተቃዋሚ የፖለቲካ ማሕበር ይሆናል። ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።

አንጋፋዉ ብሔራዊ ተቃዋሚ ፓርቲ መኢአድና የቀድሞዉ ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ቅንጅት በ1997 ከፈረሰ በሕዋላ የተመሠረተዉ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ-(አንድነት) ፓርቲዎች ባለፈዉ ዕሁድ ከደረሱበት ለመድረስ ዓመታት ተጉዘዋል።

ጉዞዉ በሥምምነት በልዩነትም፤ በወዳጅነት፤ በመወቃቀስም የተሞላ ነበር። የሁለቱ ፓርቲዎች ባለሥልጣናትም ሲደራደሩ-ሲፋረሱ፤ ሲወያዩ፤ ሲወቃቀሱ ብዙ ወራት አስቆጥረዋል። አሁን ግን፤ በቅርቡ በተደረገዉ ድርድር የአንድነትን መልዕክተኞች የመሩት የፓርቲዉ ዋና ፀሐፊ አቶ ስዩም መንገሻ እንደሚሉት የመዋሐዱ ድርድር ባስተማማኝ ዉል ተቋጥሯል።

መኢአድ ከዚሕ ቀደም ለብሔር፤ ብሔረሰብ መብት ከቆሙ ፓርቲዎች ጋር ለመወሐድ ሲያቅማማ ነበር። አንድነት ባንፃሩ የብሔር፤ ብሔረሰብ የፖለቲካ ፓርቲዎችን በአባልነት ያቀፈዉ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ፤ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ወይም ግንባር አባል ነዉ። የመኢአድን ባለሥልጣናት ለማነጋገር በተደጋጋሚ ያደረግነዉ ሙከራ ለጊዜዉ አልተሳካልንም። አንድነት በኩል ግን አቶ ስዩም እንዳሉት ፓርቲያቸዉ የመድረክ አባል መሆኑ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር እንዳይዋሐድ አይከለክለዉም።

Demonstration der UDJ- Unity for Democracy and Justice Party Party in Addis Abeba, Äthiopien
ምስል DW

የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተቃዋሚ-ይባሉ ገዢ፤ ያገር ዉስጥ ይሁኑ የዉጪ ለመተባባር፤ ግንባር ለመፍጠር፤ ለመዋሐድ ሲዋዋሉ፤ መዋዋላቸዉ በተነገረ ማግሥት መለየያየት፤ መጣላት መወቃቀሳቸዉ ከመደጋገም አልፎ-ተለምዷል። አሁን ለመዋሐድ የተፈራረሙት ፓርቲዎች ባንድ-ወይም በሌላ ሥም ይጠሩ እንጂ ከዚሕ ቀደም ለመቀናጀት መስማማታቸዉን ባስታወቁ ማግስት መበተናቸዉን ያወጁ ነበሩ። ያለፈዉ ላለመደገሙ ለጊዜዉ ማረጋገጫ የለም። ካለም አቶ ስዩም «ተምረናል» ያሉት ነዉ።

በሥምምነቱ መሠረት አቶ ሥዩም እንዳረጋገጡት ዉሕደቱ በአንድ ወር ጊዜ ዉስጥ ይጠናቀቃል።

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ