1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመንግስታቱ ጦር በጋዳፊ ላይ እርምጃ ጀመረ

ቅዳሜ፣ መጋቢት 10 2003

የምዕራቡና የአረቡ ዓለም መሪዎች በሊቢያ ጦር ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመዉሰድ ፓሪስ ላይ ተወያይተዉ አስቸኳይ ወታደራዊ እርምጃ ለመዉሰድ ተስማሙ። የፈረንሳዪ ፕሪዝደንት ሳርኮዚ የአገራቸዉ አየር ሃይል ጋዳፊን ለማጥቃት ዝግጁ መሆኑን አስታዉቀዋል።

https://p.dw.com/p/RAnR
የምዕራቡና የአረቡ ዓለም መሪዎች በሊቢያ ጦር ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመዉሰድ ፓሪስ ላይ ሲወያዪምስል dapd

የሊቢያዉ አንባገነን መሪ ሞአመር ጋዳፊ በበኩላቸዉ የተባበሩት መንግስታትን ዉሳኔን እንደማይቀበሉ ገልጸዋል። «ሊቢያ የሊቢያዉያን ናት እንጂ የናንተ አይደለችም! የጸጥታ ምክር ቤቱ ያሳለፈዉ የበረራ እገዳ ዉሳኔም አይሰራም» ሲሉ ሙአመር ጋዳፊ በቃል አቀባዮቻቸዉ መልክታቸዉን አስተላልፈዋል። የተባበሩት መንግስታት ጸጥታዉ ምክር ቤት በሊቢያ የበረራ እገዳ አዉጆ አንባገነኑን ጋዳፊ ተጥንቀቅ ሲል አንድ የሊቢያ አዉሮፕላን በህዝባዊ አማጽያን እጅ ስር ባለችዉ ቤንጋዚ ከተማ ላይ ተመቶ መዉደቁ ታይቶአል። የሊቢያ ህዝብ ከኔ ጋር ይሞታል የሚሉት ጋዳፊ በበኩላቸዉ አልቃይዳን እየወጋሁ ነዉ እያሉ ህዝባቸዉን በቀጣይ መደብደባቸዉን ቀጥለዋል። የአርባ ሁለት አመት የአንባገነናዊ በትረ ስልጣናቸዉ ምናልባትም በቀናት ሳይሆን በሰአታት ዉስጥ ግባተ መሪቱ ሳይፈጸም እንደማይቀር የምዕራባዉያኑ የብዙሃን መገናኛዎች በመዘገብ ላይ ናቸዉ። አንባገነኑ የሊቢያ መሪ የሙአመር ጋዳፊ ባለስልጣናት ከአለማቀፉ የጸጥታዉ ምክር ቤት ዉሳኔ ወዲህ በተለያየ ዘዴ ምዕራባዉያኑ እንዳይደርሱባቸዉ እየጣሩ ነዉ፣ የተሳካላቸዉ ግን አይመስልም። ጋዳፊም በበኩላቸዉ አገራቸዉን የወረረዉን የአልቃይዳን አሸባሪ ሃይል እየደበደብኩ ነዉ እያሉ የንጹሃንን ደም በማፍሰስ ለበትረ ስልጣናቸዉ በመታገል ላይ ናቸዉ። የሊቢያ ህዝብ መቶ በመቶ ከኔ ጋር ነዉ ህይወቱንም ለኔ ይሰዋል የሚሉት ጋዳፊ የዉጭ ሃይል በአገራቸዉ የዉስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባት እንደሌለበት በቃል አቀባያቸዉ በኩል አስጠንቅቀዋል። በሌላ በኩል የሊቢያዉ የነዳጅ ማምረቻ ሚኒስትር በሊቢያ በነበረዉ ዉጥረት ሰበብ ወደ የአገራቸዉ የተመለሱ ምዕራባዉያን የነዳጅ ኩባንያዎች በሊቢያ ሰላም ስለወረደ ወደ ሊቢያ ተመልሰዉ ስራቸዉን እንዲቀጥሉ አለበለዝያ ኮንትራቱን ለህንድ እና ለቻይና እንደሚሰጡ ገልጸዋል። ቻይና እና ህንድ በበሊቢያ የበረራ እገዳ ለማጽደቅ አለማቀፉ የጸጥታ ምክር ቤት ዉሳኔ ላይ በድምጸ ታቅቦ ካለፉት አምስት አገሮች መካከል ይገኛሉ።

Präsident Nicolas Sarkozy Libyen-Sondergipfel Elysee-Palast Paris Uno-Einsatz gegen Libyen NO FLASH
የተ.መ.ድ ሊቢያ ላይ የሃይል እርምጃ እንዲጀምር ፓሪስ ላይ ያጸደቁት የመንግስታት መሪዎችምስል AP

ይህ በንዲህ እንዳለ የምዕራቡና የአረቡ ዓለም መሪዎች በሊቢያ ጦር ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመዉሰድ ፓሪስ ላይ በመወያየት ላይ ሳሉ የፈረንሳይ የጦር አዉሮፕላኖች በሊቢያ አየር ክልል መብረር መጀመራቸዉን የፈረንሳዩ የዜና አገልግሎት አንድ ወታደራዊ ምንጭን ጠቅሶ ዘገበ። ከዝያም ነዉ የምዕራቡና የአረቡ ዓለም መሪዎች በሊቢያ ጦር ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለመዉሰድ ፓሪስ ላይ ተወያይተዉ እንደጨረሱ የፈረንሳዪ ፕሪዝደንት ኒኮላ ሳርኮዚ «ሞአመር ጋዳፊ ጥሪአችንን አልሰሙም የሊቢያ ህዝብ ደግሞ እርዳታችንን ይፈልጋል» በማለት ፓሪስ ላይ የተሰበሰቡት መሪዎች በሞአመር ጋዳፊ ላይ ወታደራዊ እርምጃ ለማካሄድ መወሰናቸዉን ያስታወቁት።

አዜብ ታደሰ
መስፍን መኮንን