1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመንግሥት በጀት ያለማፅደቅ አጣብቂኝ በአሜሪካ

ረቡዕ፣ ጥቅምት 6 2006

በዩናይትድ ስቴትስ የመንግሥት በጀት ሳይፀድቅ ሣምንታት መቆጠሩ በሀገሪቱ ብሎም በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚያስከትለው ተፅዕኖ ምን ይመስላል? የዛሬው የኢኮኖሚው ዓለም መሰናዶዋችን የሚያተኩርበት ርዕስ ነው።

https://p.dw.com/p/1A0N7
ምስል Reuters

ዲሞክራቶቹን ከሪፐብሊካኖች ጋር ለሣምንታት እንዳፋጠጠ ቆይቷል፤ እስካሁን ድረስ ያልፀደቀው የዩናይትድ ስቴትስ የመንግስት በጀት። በሀገሪቱ በርካታ የመንግሥት መስሪያ ቤቶች እንዲዘጉም አስገድዷል፤ ይኸው የበጀት ንትርክ። በዛሬው ከኢኮኖሚው ዓለም መሰናዶዋችን የዩናይትድ ስቴትስ የመንግሥት በጀት አሁንም ድረስ ያለመፅደቁ በሀገሪቱ ብሎም በዓለማችን ላይ ምን አይነት ተፅዕኖ ያስከትላል? በስፋት የምንቃኘው ይሆናል።

ዩናይትድ ስቴትስ ከባድ አጣብቂኝ ውስጥ ነው የወደቀችው። ዲሞክራቶች እና ሪፐብሊካኖች መስከረም 21 ቀን፣ 2006 ዓም መፅደቅ የነበረበትን የሀገሪቱ በጀት ለማፅደቅ አሁንም ድረስ ከስምምነት ላይ ሊደርሱ አልቻሉም። በርካታ የመንግስት መስሪያ ቤቶች እንዲዘጉ ያስገደደው ይህ የአሜሪካ በጀት ይዘት ምን ይመስላል? የዋሽንግተኑ ወኪላችን አበበ ፈለቀ ማብራሪያ አለው።

ከአበበ ጋር ወዳደረግነው ቃለ መጠይቅ እንመለሳለን። ከእዛ በፊት እስኪ የጀርመን ጥናትና ምርምር ተቋም ኃላፊ ማርሴል ፍራትስቼር የሚሉትን እናዳምጥ።
ሪፐብሊካኖች እና ዲሞክራቶች የሀገሪቱን የመንግስት በጀት አስመልክተው የገቡበት እሰጥ አገባ በነገው ዕለት መፍትሄ ሊበጅለት ይችል ይሆናል ሲሉ ግምታቸውን አስቀምጠዋል።

«ዩናይትድ ስቴትስ ሐሙስ ዕለት በቃ የመክፈል አቅም የለኝም በማለት የምታውጅ አይመስለኝም። ምክንያቱም እንዲህ አይነቱ ርምጃ ወደፊት የሚያስከፍለው ወጪ እንዲህ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፤ ልክ የዛሬ አምስት ዓመት ግድም በሌህማን ባንክ ላይ ከደረሰው የበለጠ ነው የሚሆነውና። ስለእዚህ እንዲህ መሰሉ ርምጃ በዩናይትድ ስቴትስ ምጣኔ ሀብት፣ እንዲሁም በዓለም ኢኮኖሚ ላይ የሚያስከትለው ድቀት ዋዛ አለመሆኑን ሰዉ አስቀድሞ ሳይገነዘበው አልቀርም ብዬ አስባለሁ። ይህ አደገኛ ጨዋታ በመሆኑ በቅርቡ መቋጫ ይበጅለታል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበታል።»

ይህ በዲሞክራቶቹ እና
ሪፐብሊካኖቹ መካከል የተነሳው በጀት የማፀደቅ እሠጥ አገባ የሚያስከትለው ጣጣ እንዲህ በቀላሉ የሚገለፅ አይደለም። የአሜሪካን መንግሥት በጀት እስካሁን ባለማፅደቁ መንግስት መደበኛ በጀት እንዳይኖረው መሰናክል መፍጠሩ አልቀረም። አበበ ፈለቀ በበጀት ያለመፅደቅ የተነሳ የተከሰተውን ችግር እንዲህ ያብራራል።

የጤና ዋስትናን ጨምሮ ሌሎች ዓመታዊ በጀት የሚያስፈልጋቸው ዕቅዶች በዲሞክራቶቹና ሪፐብሊካኖቹ መካከል ንትርክ በማስከተሉ በዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ከተከሰተው በጀት ያለማፅደቅ ችግር ባሻገር በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚያስከትለው ተፅዕኖ ከባድ እንደሚሆን ተገምቷል። ለአብነት ያህል በጃፓን የፋይናንስ ሚንስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር የሆኑት ታሮ አሶ የአሜሪካ የመንግስት በጀት ያለመፅደቅ በዓለም አቀፍ ደረጃ ችግር ሊያስከትል እንደሚችል ትናንት ለጋዜጠኞች ገልፀዋል።

ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ ከታች ያለውን የድምፅ ማጫቻ ይጫኑ

ካፒቶል፣ ዋሽንግተን ዲሲ
ካፒቶል፣ ዋሽንግተን ዲሲምስል picture-alliance/AP
የመንግሥት መስሪያ ቤት መዘጋትን በመቃወም
የመንግሥት መስሪያ ቤት መዘጋትን በመቃወምምስል Reuters

ማንተጋፍቶት ስለሺ




ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ