የመመረቂያ ፁሁፍ እና የሰውን ሀሳብ መስረቅ
ዓርብ፣ የካቲት 8 2005ሻቫን ከ 30 አመት በፊት በፃፉት የዶክትሬት የመመረቂያ ፁሁፍ ላይ የሰውን ሀሳብ የራሳቸው አስመስለው በፁሁፋቸው አስፍረዋል በሚል ክስ፤ የዶክትሬት ማዕረጋቸውን ተገፈዋል። ይህም ከሚንስትርነት ስራቸውም ለመባረር ዳርጓቸዋል።
እስካለፈው ሳምንት በጀርመን የትምህርት ሚኒስትርነት ሲያገለግሉ የቆዩት አኔተ ሻቫን፤ በተለይም ከትምህርት ጋ በተያያዘ መከሰሳቸው ይህም እስከ የዶክትሬት ማዕረግ መነጠቅና ከስራ መባረር መዳረጉ፤ ዮሀንስ ሀጎስ ለጉዳዩ የበለጠ ትኩረት ሰጥቼ እንድከታተለው አድርጎኛል ይላል። ወጣቱ በጀርመን ድሬስድን ዩንቨርስቲ በአሁኑ ሰዓት በውሃ ምንድስና ላይ ለ3ኛ ዲግሪው ( PHD) የመመረቂያ ጥናት እየፃፈ ይገኛል። ተሞክሮውን አካፍሎናል።
ባለማወቅ፣ በቸልተኝነት ወይንም ይህ አጠቃላይ እውቀት ነው በማለት አንድን ሀሳብ ከሌላ ቦታ የመነጨ መሆኑን ያለመጥቀስ ሁኔታ ይታያል። ለመሆኑ መቼ ነው አንድ ሰው የራሱን ያልሆነን ጥናት ወይንም ሀሳብ ምንጭ ሳይጠቅስ አቀረበ የምንለው? በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የሶይሲዮሎጂ ተባባሪ ፕሮፌሰር የሆኑት - ዶክተር የራስ ወርቅ አድማሴ በዚህ ላይ መልስ ሰጥተውናል።
ዶክተር የራስ ወርቅ በየጊዜው የተለያዩ የመመረቂያ ፁሁፎችን ማንበብ ግድ ይላቸዋል። አልፎ አልፎም «ይህን አረፍተ ነገር የት ነበር ያነበብኩት» የሚለው ጥርጣሬ ያድርባቸዋል።
የራስ ያልሆነን ጥናት እንደ ራስ አድርጎ ማቅረብ ፤ ማዕረግን እስከመነጠቅ እንደሚያደርስ በቅርብ ጊዜ እዚህ ጀርመን ውስጥ ብቻ በሁለት ፖለቲከኞች ላይ ታይቷል። የጀርመኗ ሚኒስትር የመመረቂያ ፁሁፍ ተመሳክሮ ስህተቱ የተገኘው ለ ሶስት አስርተ ዓመታት በመቀመጡ ነው። ይህም በኢትዮጵያ ይደረጋል። ግን ዶክተር የራስ ወርቅ እንደገለፁልን፤ ለሁሉም ፁሁፎች አይደለም።
የአንድን እጬ ተመራቂ ፁሁፍ ለማመሳከር ኢትዮጵያ ውስጥ ምን ከባድ ያደርገዋል? ለዚህ እና ለሌሎች ጥያቄዎች ዶክተር የራስ ወርቅ ጠቃሚ ሀሳቦች አካፍለውናል። ከድምፅ ዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሀመድ