የላይቤሪያ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ
ዓርብ፣ ጥቅምት 3 2010
ከእርስበርስ ጦርነት ተላቃ ላለፉት 12 ዓመታት ተረጋግታ በቆየችዉ ላይቤሪያ የፕሬዝዳንታዊ ምርጫ የመጨረሻዉ ዉጤት በ15 ቀናት ዉስጥ ይፋ እንደሚሆን ይጠበቃል።
ሞዕራብ አፍሪካዊቷ ሀገር ላይቤሪያ በቅርቡ የስልጣን ዘመናቸዉን የሚያጠናቅቁትን ፕሬዝዳንት ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍን ለመተካት ባለፈዉ ማክሰኞ ምርጫ አካሂዳለች። በዚህ ብሄራዊ ምርጫ የቀድሞዉን የእግር ኳስ ኮከብ ጆርጅ ዊያን ጨምሮ 20 እጩዎች ለፉክክር ቀርበዋል። በትናንትናዉ ዕለት ይፋ የሆነዉ የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ጊዜያዊ ዉጤት እንደሚያሳየዉ ሁለት እጩዎች ብቻ በመምራት ላይ ይገኛሉ።። የቀድሞዉ የእግር ኳስ ኮከብ ጆርጅ ዊያና ምክትል ፕሬዝዳንቱ ጆሴፍ በካይ ።
ምክርቤት ለዲሞክራሲያዊ ለዉጥ ፓርቲ / CDC/ን ወክሎ የተወዳደረዉ ጆርጅ ዊያ ከ15 የሀገሪቱ ግዛቶች በ14 ቱ ድል ቀንቶታል ተብሏል። ከአንድነት ፓርቲ/unity party/ ምክትል ፕሬዝዳንት ጆሴፍ በካይ ደግሞ በመኖሪያ አካባቢያቸዉ በሎፋ ግዛት አብላጫ ድምፅ ማግኘታቸዉን የኮሚሽኑ ሊቀመንበር ጀሮሚ ካኩያ ገልጸዋል።
«እስካሁን በአብዛኛወቹ ምርጫ ጣቢያወች ሁለቱ ፓርቲወች እየመሩ ነዉ።ጆሴፍ ኒዶማህ ከአንድነት ፓርቲ፣ጆርጅ ዊሃ ከምክርቤት ለዲሞክራሲ ለዉጥ ፓርቲ።»
የአሸናፊዎቹ ፓርቲወች የCDC ደጋፊወችም ከወዲሁ ደስታቸዉን እየገለጹ ቢሆንም አንዳንዶቹ ደግሞ ዉጤቱን ለመቀበል መቸገራቸዉን ተናግረዋል። ዊኒታ ግሌይ የተባሉ መራጭ እንደሚሉት ይፋ የተደረገዉ ዉጤት ለሳቸዉ የማይታመን ነዉ።
«የምርቻ ዉጤቱን ተከታትየዋለሁ።ነገር ግን ምንም ጥሩ ስሜትና እርካታ አልተሰማኝም።እኔ ከብሩም ሲኪኒ ጋር ነኝ።ምን አይነት ሰወችን እንደምናወራ ኢናዉቃለን። ይመርጡናል ብለን የምንጠብቃቸዉን ሰዎች እናዉቃለን።ምን አይነት ሰዎች ድምጽ እንደሰጡን እናዉቃለን።ነገር ግን የጠበቅነዉን አይነት ዉጤት አላገኜንም።»
የምርጫ ኮሚሽኑ ሊቀመንበር እንደገለፁት እስካሁን ቆጠራ የተካሄደበት ከአጠቃላይ የድምፅ መጠን 30 በመቶ ብቻ ነዉ። እናም ይህ የምርጫ ዉጤት ከጠቅላላዉ የድምፅ መጠን አነስተኛዉን የሚወክል በመሆኑ ደጋፊዎችና እጩዎች አስቀድመዉ ድልን ከማወጅ እንዲቆጠቡና የመጨረሻዉን ዉጤት በትዕግስት እንዲጠብቁ አሳስበዋል።
አንዳንድ የሀገሪቱ የፓለቲካ ፓርቲወችና ደጋፊወችም ከወዲሁ ቅሬታ ማሰማት ጀምረዋል። ወጥ ያልሆነ የድምፅ ቆጠራና የምርጫ ጣቢያዎች ዘግይቶ መከፈት ከቅሬታዎቹ መካከል ይገኙበታል። የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽኑም መሰል ቅሬታዎችን ለመቀል ዝግጁ መሆኑን ገልጿል።
ምርጫዉን የታዘበዉ የካርተር ማዕከል እንዳስታወቀዉ በምርጫ መዝገብ አያያዝ ችግር፤ እንዲሁም ረጃጅም የመራጭ ሰልፎችን መመለከቱን ገልጿል። የድምጽ ቆጠራዉ እስኪጠናቀቅም የማጠቃለያ ግምገማ ከመስጠት መቆጠቡን አመልክቷል። ዉጤቱ ምንም ይሁን ምን ላይቤሪያ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ በዲሞክራሲያዊ መንገድ ከተመረጠ አንድ ፕሬዝዳንት ወደ ሌላዉ እንደምትሸጋገር ማዕከሉ እምነቱን ገልጿል።
የተረጋጋና ሰላማዊ ምርጫ በማካሄዱ ለመራጩ ህዝብ ምስጋናና ያቀረቡት ደግሞ የአዉሮጳ ትብረት ታዛቢ ማሪያ አሬና ናቸዉ። እንደ ታዛቢዋ ምርጫዉ ሕጋዊ ማዕቀፍን ተከትሎ የተካሄደ ነበር ።
« ከገግጭት በሁዋላ ላይቤሪያዉያን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠሩቸዉ የመጀመሪያወቹ ምርጫወች የሀገሪቱን የሽግግር ሂደት ከፍ ያከፍ አድርገዋል።ምርጫወቹ በብዝሃ ፓርቲና የመገናኛ ብዙሃን ፣በከፍተኛ የህዝቡና የሲብሉ ማህበረሰብ ቁርጠኝነት የታገዘ ናቸዉ።ዓለም አቀፍ ደረጃን በጠበቀ የህግ ማዕቀፍም የተዳኙ ናቸዉ»
የሀገሪቱ ሕገ መንግስት በሚደነግገዉ መሠረት ምርጫዉ በተካሄደ በ15 ቀናት ዉስጥ ዉጤቱ ይፋ ይደረጋል። በጎርጎሮሳዊዉ 2005 ዓ/ም ሰላማዊ በተባለ ሽግግር ወደ ስልጣን የመጡት ኤለን ጆንሰን ሲርሊፍም ከ12 አመታት የስልጣን ቆይታ በኋላ በመጭዉ ጥር ስልጣናቸዉን ያስረክባሉ። ላይቤሪያ ነፃነቷን ከተቀዳጀች ከጎርጎሮሳዉያኑ 1847 ወዲህ የመጀመሪያዋን የአፍሪካ የሴት ፕሬዚዳንት ሲርሊፍን ጨምሮ 24 ፕሬዝዳንቶችን አስተናግዳለች።
ፀሐይ ጫኔ
ሽዋዬ ለገሰ