1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ መንግሥትና የዲያስፖራዉ ግንኙነት

እሑድ፣ ሰኔ 11 2009

የኢትዮጵያ መንግሥት እና የዲያስፖራዉ ግንኙነት እንዴት ይገመገማል? የኢትዮጵያ ዲያስፖራ የከረረ ተቃውሞ መንስዔው የአገር ውስጥ የፖለቲካ ምኅዳር መጥበብ ነው የሚሉ አሉ። ዉጭ የሚገኘዉ ተቃዋሚ ኃይላት ዓላማ ተመሳሳይ ቢመስልም ለተቃዉሞ በጋራ ሲንቀሳቀሱ ደሞ አይታይም። ምክንያቱ ምንድን ነዉ?

https://p.dw.com/p/2eso0
Südafrika Äthiopien Solidaritätsbekundung
ምስል DW/M. Ayele

ዉይይት፤ የኢትዮጵያ መንግሥትና የዲያስፖራዉ ግንኙነት

ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን፤ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የሚያካሂዱት ተቃዉሞ እየጨመረ መጥቶአል። በተለይ የመንግሥት  ከፍተኛ ባለስልጣናት በዉጭ ሃገራት ጉብኝት ለማድረግ በተጓዙ ቁጥር ሰልፍ ይወጣባቸዋል። አንዳንዴም ስድብ እና ጉንተላ ይከተላቸዋል።

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ ተቃዋሚዎች የኢትዮጵያ መንግሥት ሹማምንት ይገኙባቸዋል በተባሉ ሆቴሎችም ሆነ የመገበያያ ስፍራዎች በመገኘት «ተቃዉሞአችንን ይገልፅልናል፤ የመንግሥትን በደል ያጋልጥልናል» ባሉበት መንገድ የተቃውሞ ድምጻቸውን በተደጋጋሚ እያሰሙ ናቸው፡፡ በስዊዘርላንድ በቅርቡ የዓለም የጤና ድርጅት ዳይሬክተር ሆነዉ የተመረጡት የቀድሞዉ የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይና የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖምን  እና በጠቅላይ ሚኒስትር የኃይለማርያም ደሳለኝ የእስራኤል ጉብኝት ወቅት የተከሰቱት የቅርብ ጊዜዎች ማሳያ ናቸዉ። መንግሥት በዉጭ ሃገራት የሚኖሩ ተቃዋሚ ኢትዮጵያዉያንን ፀረ-ልማትና ፀረ-ሠላም ሲል ይፈርጃቸዋል። በዉጭ ሀገር የሚታየዉን ተቃዉሞ አመፅን የሚሰብክ እና ሥነ-ምግባርም የጎደለዉ ሲል ይደመጣል።

የኢትዮጵያ መንግሥትና የዲያስፖራዉ ግንኙነት የዛሬዉ ዉይይታችን ትኩረት ነዉ።  በዚህ ላይ ሃሳባቸዉን እንዲያካፍሉን አራት እንግዶችን ጋብዘናል። ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ፤  የአፍሪካ የስትራቴጂና ጸጥታ ተቋም ዋና ስራ-አስፈጻሚ ፤ አቶ በጋሻዉ ከበደ፤ በካናዳ ቶሮንቶ የኢህአዴግ ደጋፊዎች ማኅበር አባል፤ አቶ በላይነህ ተሾመ፤ በበርሊን ነዋሪ የሆኑት ለ 10ተ ዓመታት ከተማሪዉ ንቅናቄ ጀምሮ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉዳይ ላይ በተለያዩ መስኮች አስተዋጽኦ እያደረጉ የሚገኙት በበርሊን የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ተወካይና የኢህአዴግ ተቃዋሚ እንዲሁም ከአዲስ አበባ የኢንተርኔት አምደኛዉ በፍቃዱ ኃይሉ ናቸዉ። ሙሉዉን ዉይይት የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።

 

አዜብ ታደሰ

ልደት አበበ