1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉይይት፤ ኢትዮጵያ ዳግም ተቃዉሞ፤ ዳግም ግድያ

እሑድ፣ ታኅሣሥ 17 2008

ለወራት ዉስጥዉስጡን ሲብላላ የቆየዉ ተቃዉሞ ከአንድ ወር በፊት ፈንድቶ ኢትዮጵያን እየናጣት ነዉ።በቆየ ፖለቲካዊ፤ አስተዳደራዊ፤ ቅሬታዎች የሚገፋ የሚመስለዉን ተቃዉሞ ለማመቅ በዘመተዉ ፀጥታ አስካባሪ እና በተቃዋሚዎች መካከል በተቀሰቀሰዉ ግጭት ከ75 እስከ 85 የሚደርሱ ሰዎች መገደላቸዉን የመብት ተሟጋቾችና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች አስታዉቀዋል።

https://p.dw.com/p/1HTiE
ምስል Oromia Media Network

ኢትዮጵያ ዳግም ተቃዉሞ፤ ዳግም ግድያ

ኢትዮጵያ ከጦርነትም፤ ከምዕራባዉያን ጫና፤ መገለልም ተላቃ በልማት መገስገሷ መዓልት ወሌት በሚዘገብ፤ በሚነገር፤ በሚተነተንበት መሐል የብዙ ሚሊዮን ረሐብተኞች፤ የሚሊዮን ስደተኞች ሐገር የመሆኗ ሐቅ በርግጥ ብዙ እንዳስተዛዘበ፤ እንዳነጋገረ ነዉ።

ረሐብ የጠናበት ሕዝቧ ከከፋ ችግር የሚድንበት ሥልት፤ ብልሐት እና እርምጃ በቅጡ ሳይታወቅ ከሠሜን እስከ መሐል ወይም (ከአማራ እስከ ኦሮሚያ) ሕይወት ከሚያጠፋ፤ አካል፤ ሐብት-ንብረት ከሚያወድም ቀዉስ ተዘፍቃለች።የጠናዉ የመሐሉ ወይም የኦሮሚያዉ ነዉ።

«አዲስ አበባን ከአጎራባች ከተሞችና ቀበሌዎች ጋር የሚያስተሳስር ዕቅድ የተቀናጀ ማስተር ፕላን»-ብለዉታል አቃጆቹ) መነደፉ ከተሰማበት ካንድ ዓመት በፊት ጀምሮ በርዕሠ-ከተማይቱ ዙሪያ የሚኖረዉ ሕዝብ በተለይ ተማሪዎች ዕቅዱን ወይም ሐሳቡን በተለያየ መንግድ ግን በግልፅ ተቃዉመዉታል።ብዙ ታዛቢዎች እንደሚሉት የኢትዮጵያ መንግሥት የዕቅዱን ትክክለኛ አላማ ለባጉዳዩ ሕዝብ ከማስረዳት፤የተቃዋሚዎችን ጥያቄ ከመስማት፤ ወይም ደግሞ ዕቅዱን ከመሠረዝ ይልቅ ዕቅዱን የማይቀበሉትን ወገኖች በማዉገዝ፤ ማስፈራራት አንዳዴም በማሰር ላይ ነበር ያተኮረዉ።

Berlin Demonstration von Oromo-Aktivisten
ምስል DW/H. Kiesel

ለወራት ዉስጥዉስጡን ሲብላላ የቆየዉ ተቃዉሞ ከአንድ ወር በፊት ፈንድቶ ኢትዮጵያን እየናጣት ነዉ።በቆየ ፖለቲካዊ፤ አስተዳደራዊ፤ ፍትሐዊ ቅሬታዎች የሚገፋ የሚመስለዉን ተቃዉሞ ለማመቅ በዘመተዉ ፀጥታ አስካባሪ እና በተቃዋሚዎች መካከል በተቀሰቀሰዉ ግጭት ከ75 እስከ 85 የሚደርሱ ሰዎች መገደላቸዉን የመብት ተሟጋቾችና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች አስታዉቀዋል።

መንግሥት በሚቆጣጠረዉ መገናኛ ዘዴ ያስታወቀዉ ግን የተገደሉት ሰዎች አምስት ናቸዉ የሚል ነዉ።የቆሰለና የታሠረዉ ሰዉ ብዛት፤ የጠፋዉ ሐብት ንብረት መጠን፤ የተስተጓጎለዉ ሥራና ትምሕርት ጉድለት በዉል አያታወቅም።

ከወሎንኮሚ፤ ጊንጪ፤ጀልዱ እስከ ኢታያ፤ከመዳ ወለቡ እስከ ነጆ፤ጉሊሳ፤ ደንቢ ዶሎ፤ እስከ ከሐሮማያ፤ ምዕራብ ሸዋ፤ወለጋ፤አርሲ፤ ባሌና ሐረርጌ ላይ የተቀጣጠለዉ ግጭት፤ተቃዉሞና ቀዉስ ዉጪ የሚኖሩ ኢትዮጵያዉናንን ለአደባባይ የተቃዉሞ ሠልፍ አሳድሟልም።ሑዩማን ራይትስ ዋች የተሰኘዉ ዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋች ድርጅት የመንግሥትን እርምጃ ሲያወግዝ፤ ሲፒጄ ቢያንስ የአንድ ጋዜጠኛን መታሰር ተቃዉሟል፤ የዩንያትድ ስቴትስ ዉጪ ጉዳይ ሚቴር «በጣም አሳሳቢ» ብሎታል።

Berlin Demonstration von Oromo-Aktivisten
ምስል DW/H. Kiesel

የአሳሳቢ ወይም የአሳዛኙ ቀዉስ ሰበብ ምክንያት፤ደረጃና መፍትሔዉ የዛሬ ዉይይታችን ትኩረት ነዉ።

ነጋሽ መሐመድ

ማንተጋፍቶት ስለሺ