ወጣቶች በስጋት ሲኖሩ
ዓርብ፣ ታኅሣሥ 17 2007በአምስት ሰዎች ታፍና ተወስዳ ፤ በወሲባዊ ጥቃት ህይወቷ ስላለፈው ሃና ላላንጎ የሰማ ኢትዮጵያዊ ፤ አዝኗል፣ ለራሱ ወይም ወላጅ ከሆነ ደግሞ ለልጆቹ ሰግቷል።
ሃና በደረሰባት ወሲባዊ ጥቃት ህይወቷ ማለፉ ከተሰማ በኋላም በሌሎች ወጣቶች ላይ ወሲባዊ ጥቃት መድረሱ ተሰምቷል። በሰዎች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን በቅርበት የሚከታተሉ ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ እቤት ውስጥ ተዳፍነው የሚቀሩት ጥቃቶች ቁጥር በይፋ ከሚታወቀው እጅግ ከፍተኛ ነው። የ 18 ዓመቷ ሔርሜላ ታፈሰ ፤ የአዲስ አበባ ነዋሪ እና የ 12ኛ ክፍል ተማሪ ናት። መንገድ ላይ ብቻዋን መሄድ እንደማያስተማምናት ገልፃልናለች።
ወጣቶች በየሄዱበት ጥቃት እንዳይደርስባቸው ሲፈሩ ራሱን የቻለ ስነ ልቦናዊ ጭንቀት እንደሚፈጥር የስነ ልቦና ባለሙያዎች ይናገራሉ። ወ/ሮ ማርያ ሙኒር፤ የህግ ባለሙያ እና የሴቶች ማረፊያ እና ልማት ማህበር ዳሬክተር ናቸው። ስራቸው ጥቃት ከደረሰባቸው በርካታ ወጣት ሴቶች ጋር ያገናኛቸዋል።
በተለይ ወደ ገጠራማው አካባቢ ሲሄድ ልጆች ከ አንድ እስከ 2 ሰዓት የእግር መንገድ ተጉዘው ነው ትምህርት ቤት የሚደርሱት፤ መንገድ ላይ ብዙ ነገር ይገጥማቸዋል።መምህር መንግሥቱ ወልደ ማርያም በደቡብ ክልል ከፋ ዞን ውስጥ ቀና የምትባል ወረዳ ከ5 -7ኛ ክፍል ተማሪዎችን ያስተምራሉ። እሳቸው በሚኖሩበት አካባቢ ወሲባዊ ጥቃቶች ጨርሶ ይፋ አይሆኑም ለማለት ያስደፍራል ይላሉ።
ለመሆኑ ወሲባዊ ጥቃት ከየት ይጀምራል? ወጣቶች ወሲባዊ ጥቃት ምን ያህል ያሰጋቸዋል? ጥቃት ሲደርስባቸው ምን ማድረግ አለባቸው? በእነዚህ ነጥቦች ላይ በወጣቶች ዓለም ዝግጅት ተወያይተናል። ዘገባውን በድምፅ ያገኛሉ።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሐመድ