1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ወጣት በጎ ፈቃደኞች

ዓርብ፣ ሰኔ 10 2008

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በኢትዮጵያ በተለይም በአዲስ አበባ ወጣቶች በበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት ላይ ሲሰማሩ እየተስተዋለ ነው። አብዛኞቹ የግብረ-ሰናይ ሥራዎችን ይመርጣሉ አለያም ሌሎች አይነት የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች አልተለመዱም።

https://p.dw.com/p/1J8sm
Pflegeheim in Addis Abeba Meqedonya
ምስል DW/Y. Gebreegziabher

ወጣት በጎ ፈቃደኞች

የ24 አመቱ ወጣት ራጄ ዲንሳ ራሳቸውን ችለው መጸዳዳት እና መንቀሳቀስ የማይችሉ አረጋውያን እና የአዕምሮ ሕሙማን የተጠቀሙባቸውን አንሶላዎች እና ብርድ ልብሶች ያጥባል። በራሳቸው መመገብ የማይችሉትን ይመግባል። ይህ በቀን የ24 ሰዓት በሳምንት የ7 ቀናት ሥራው ነው። ራጄ ዲንሳ የበጎ ፈቃድ አገልጋይ ነው።

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በበጎ ፈቃደኝነት ማገልገል በወጣት ኢትዮጵያውያን ዘንድ እየተለመደ መጥቷል። ወጣቶች ለሕጻናት እንደ እርሳስ እና ደብተር የመሳሰሉ የመማሪያ ግብዓቶች ሲያሰባስቡ ይስተዋላል። ላጡ እና ለተቸገሩ አልባሳት ማሰባሰብም የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እንደ ባህል ባልተለመደበት አገር ሲስፋፋ እየታየ ነው። ነብዩ ኢሳያስ የማኔጅመንት ኢንፎርሜሽን ሲስተም ባለሙያ ነው። በአንድ የመንግስት ተቋም ውስጥ የሚያገለግለው ነብዩ በሜቄዶንያ የአረጋውያን እና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል በሙያው እና በቃል አቀባይነት ያገለግላል።በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪውን የሠራው ወጣት ራጄ ዲንሳም ይሁን ነብዩ ኢሳያስ የበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት መንፈሳዊ እርካታ እንዳለው ይናገራሉ።

ወጣት የውብነሽ ከበደ እንደ ራጄ ዲንሳ እና ነብዩ ኢሳያስ የበጎ ፈቃድ አገልጋይ ናት። በአዲስ አበባ አውራ ጎዳናዎች፤ የመንግስት እና የግል ተቋማት እየተዘዋወረች ሌሎች ሰዎች በትርፍ ጊዜያቸው ድጋፍ እንዲያደርጉ ትወተውታለች። ይህ ዛሬ ነው። ወጣቷ በበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት ላይ ከመሰማራቷ በፊት ወደ አረብ አገራት የመሄድ ፍላጎት ነበራት።
ራጄ ዲንሳ ትምህርቱን ትቶ ሙሉ ጊዜውን መስዋዕት ያደረገለት የበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት መልሶ የከፈለው ይመስላል። የ24 አመቱ ወጣት ምርቃት ቀለቡ ሆኗል።

ኢሳያስ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በትምህርትም ሆነ በሥራ ላይ ቢሆኑም እንኳ በበጎ ፈቃደኝነት ላይ ለመሠማራት ቁርጠኝነት ብቻ ያሻቸዋል የሚል እምነት አለው።የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ኢትዮጵያ ዉስጥ ከግብረ-ሰናይ ሥራዎች ጋር ብቻ የተቆራኘ ይመስላል። በሌሎች አገሮች የበጎ ፈቃድ አገልጋዮች በአደጋ ጊዜ ሠራተኝነት፤ የጥገናና እና የማማከር ሥራዎች ተሰማርተው ከፍ ያለ አስተዋጽዖ ሲያበረክቱ ይስተዋላል። የመኖሪያ መንደሮች ጸጥታን ያስጠብቃሉ፤ አውራ ጎዳናዎች፣ ወንዞች እና የከተማ ክፍት ቦታዎችን ያጸዳሉ። በሙያቸው ለመንግሥት ከክፍያ ነጻ አገልግሎት ሰጥተው የሕዝብ ገንዘብን ከወጪ ይታደጋሉ። ድንበር እና ባህር ተሻግረው የሕክምና አገልግሎት ይሰጣሉ። ስደተኞችን ቋንቋም ያስተምራሉ፤ ሥራ በማፈላለግም ይተባበራሉ። ራጄ ዴንሳ በኢትዮጵያ እየተለመደ የመጣው የበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት ማደግ አለበት የሚል እምነት አለው።

እሸቴ በቀለ
ሸዋዬ ለገሰ