1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«ወርልድ ዋይድ ዌብ»ና የ 20 ዓመት አገልግሎቱ፣

ሐሙስ፣ ነሐሴ 5 2003

በሥነ ቴክኒክ እየተራቀቀ በመጣው ዓለም ፣ በኢንተርኔት መረብ አማካኝነት መረጃዎችን ከመቅጽበት ማግኘትም ሆነ ማስተላለፍ የሚቻልበት ሁኔታ በሚገባ ነው የተመቻቸው።

https://p.dw.com/p/RfHJ
ምስል AP Graphics

የአውሮፓውያን የኑክልየር ተመራማሪ ድርጅት ፤ በፈረንሳይኛው ምህጻር (CERN) በመባል የታወቀው ዋና ጽ/ቤቱ በጀኔብ እስዊትስዘርላንድ የሚገኘው ይኸው ማህበር በአሁኑ ጊዜ ከ 20 የማያንሱ አባል መንግሥታትና 8 ታዛቢዎች ያሉት ሲሆን ፣ የተመሠረተው እ ጎ አ በ 1954 ዓ ም፤ በ 12 አባል መንግሥታት ነበር።

CERN ስሙም እንደሚያመለክተው የምርምር ትኩረቱ በፊዚክስ ላይ ነው። በዚያ የምርምር ጣቢያ ከሚሠሩ ሳይንቲስቶች መካከል አንዳንዶች በተናጠልና በህብረት በተለያዩ ጊዜያት የኖቤል ተሸላሚዎች ለመሆን በቅተዋል።

በአሁኑ ዘመን መላው ዓለም በኢንተርኔት መረጃዎችን ማስተላለፍ የሚችልበትን ምርምር CERN ውስጥ ፤ እንግሊዛዊው ሳይንቲስት Tim Berners-Lee የጀመሩት እ ጎ አ በ 1989 ዓ ም ሲሆን ፣ World Wide Web የተባለውን ይህንኑ በኮምፒዩተር መረጃ የማስተላለፊያ ዘዴ በመፈልሰፋቸውም በዚህ ረገድ የተሳካ ውጤት በማስመዝገባቸው ድርጅቱ እ ጎ አ በ1995 ዓ ም ልዩ እውቅና ሰጥቷቸዋል። በመጀመሪያ ፣ በተመራማሪዎች መካከል መረጃ ለመለዋወጥ ታስቦ የተፈለሰፈውና፣ የሠመረው WWW ፣ እ ጎ አ ነሐሴ 6 ቀን 1991 ዓ ም ፣ የጽሑፍ የድምጽና ምስል መረጃዎችን የማስተላለፍና የመቀበል፣ የኢንተርኔት አገልግሎቱን የጀመረ ሲሆን፤ ከሚያዝያ 30 ,1993 ዓ ም ጀምሮም፤ አገልግሎቱ ለሁለም ይፋ እንዲደረግ ፤ ለማንም ሰው ነጻ እንዲሆን መታወጁ የሚታወስ ነው። WWW ለህዝብ አገልግሎት መስጠት የጀመረበት 20ኛው ዓመት ባለፈው ቅዳሜ በመላው ዓለም በኮምፒዩተር ተጠቃሚዎች ዘንድ በልዩ ሁኔታ ነው ታስቦ የዋለው።

ተክሌ የኋላ

ሸዋዬ ለገሰ