«ኮንሶ ደሞዝ የለም፣ ጤና ጣብያ ተዘግተዋል» ኮሚቴ
ዓርብ፣ ነሐሴ 6 2008የህብረተሰቡ ጥያቄ ኮንሶ ራሱን የቻለ ዞን እንዲሆን ቢሆንም ጥያቄው መልስ አለማግኘቱን ጉዳዩን እንዲከታተል የተሰየመው ኮሚቴ ተናግሯል። በአሁኑ ሰዓት የክልሉ መንግስት «ጥያቄዉን ለማፈን» ከዚያም በላይ ላለፉት አራት ወራት የመንግስት ሠራተኞች በሙሉ ደሞዝ እንዳልተከፈላቸው፣ የጤና ጣብያዎችና ኬላዎችም እንደተዘጉ እንድሁም በሴፍትኔት የሚከፈለዉ የአንድ አመት ክፍያ እንዳልተፈፀመ የኮሚቴው አባል የሆኑት አቶ ገማቹ ጌንፌ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል።
በኮንሶ 11 ጤና ጣብያዎችና ወደ 52 ጤና ኬላዎች እንዳሉ አቶ ገመቹ ጠቅሶ ሁሉም ላለፉት አራት ወራት ስራ እንዳቆሙ ይናገራሉ። እንደ አቶ ገመቹ የአዉሮፓ ህብረት ለሴፍቲ ኔት መርሃ ግብር የለገሰው እርዳታም ለተቸገሩ የህብረተሰብ ክፍሎች አልደረሰም።
ለዚህ መልስ እንድሰጡን የክልሉን የኮሙኒኬሸን ጉዳዮች ሃላፊ አቶ ቃድራላ አህመድን ስንጠይቅ ጉዳዩ እንደማይመለከታቸው ይናገራሉ።
ከዚህ በተጨማሪ የክልሉ ልዩ ኃይል የሚወስዳቸዉ የድብደባ፣ የእስራትና ግድያ ርምጃዎች መቀጠሉን ፣ በቅርቡ የ11ወር ህፃን ህይወት እንዳለፈም ይናገራሉ። የመንግስት ሚድያዉም የኮንሶ ህዝብ ጥያቄን የጥቂት ግለሰቦች ጥያቄ አድርጎ አሳንሶ በማቅረብ ህዝቡ ላይ ዘምቷል ይላሉ አቶ ገመቹ ።
ይህን ጉዳይ እንዴት ትመለከቱታላችሁ ብለን የፌስቡክ ተከታታዮቻችን ስንጠይቅ አንዳንዶቹ መንግስትንና ህዝብን በተሳሳተ መረጃ አታጣሉ ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ ፣ የህዝቡ ጥያቄ መቸ ተመልሶ ያቃል። መንግስት ህዝብ ነው ፣ህዝብ ደሞ መንግስት ነው ይላል፣ ግን የሚባ,ው እና የሚሆነው ጨርሶ አይገናኝም ፤ አሁን ያለንበት ቀውስ ውስጥ ያስገባንም ይሄው ነው።>> ብለዋል።
መርጋ ዮናስ
ኂሩት መለሰ