1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኬንያ የዝሆን ጥርስ ልታቃጥል ነው

ዓርብ፣ ሚያዝያ 21 2008

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት መረጃ መሰረት ከ420,000 እስከ 650,000 ይደርሳሉ ከሚባሉት የአፍሪቃ ዝሆኖች በየዓመቱ ከ25,000 በላይ በህገ-ወጥ አዳኞች ይገደላሉ። ንያ በነገው ዕለት ከፍተኛ መጠን ያለው የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ልታቃጥል በዝግጅት ላይ ነች።

https://p.dw.com/p/1IfQA
Elfenbeinverbrennung in Kenia
ምስል DW/A. Wasike

[No title]

ናይሮቢ በሚገኘው የኬንያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ዋና ጽ/ቤት ከ100 በላይ ወጣቶች የዝሆን ቀንዶችን እያራገፉ ነው። የዱር እንስሳት ጥበቃ ሰራተኞች እና ወጣቶቹ ከጭነት መኪኖች ላይ የሚያራግፉት የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ከህገ-ወጥ ነጋዴዎች ተወርሶ በነገው ዕለት ሊቃጠል የተዘጋጀ ነው።
ኬንያ በናይሮቢ ብሔራዊ ፓርክ ልታቃጥለው የተዘጋጀችው የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ በብዛት ዓለም ከዚህ ቀደም ከተመለከታቸው ሁሉ የላቀ ነው። የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ኡኹሩ ኬንያታ በነገው ዕለት በ105 ቶን የዝሆን ጥርስ እና 1.35 ቶን የተለያዩ ዱር እንስሳት ውጤቶች ላይ እሳት ሲለኩሱ ለዓለም ጠንካራ መልዕክት ያስተላልፏሉ ተብሏል። የኬንያ የዱር እንስሳት አገልግሎት ምክትል ኃላፊ ፓትሪክ ኦሞንዲ መልዕክቱ ለህገ-ወጥ አዳኞች፤አዘዋዋሪዎች የታለመ እንደሆነ ይናገራሉ።
«ይህ ለኬንያ ታሪካዊ ክስተት ነው። ኬንያ የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ህገ-ወጥ ዝውውርን ለመዋጋት ያላትን ቁርጠኝነት ያሳያል። ልናቃጥል የተዘጋጀንው ከዝንጀሮ፤አንበሳ እና አቦሸማኔ ገዳዮች የተያዙ ሽልማቶችን ነው። እነዚህን እንስሳት መግደል ህገ-ወጥ ነው። ይህን ከፍርድ ቤት ውጪ የሚገኘውን የምናቃጥለው እሱን ለመጠበቅ ተጨማሪ ወጪ ላለማውጣት እና ተመልሶ ወደ ገበያ እንዳይገባ ለማድረግ ነው።»

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከዚህ ቀደም ህገ-ወጥ የዝሆን እና የአውራሪስ አደን በአፍሪቃ የሚታየውን ሽብርተኝነት እና ሌሎች ወንጀሎች የገንዘብ ምንጭ እንደሆነ አስታውቆ ነበር።
አንዳንድ ኬንያውያን ግን አንድ ቢሊዮን ዶላር የሚገመተውን የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ማቃጠል እርባና ቢስ እንደሆነ ይሰማቸዋል። ኬንያውያኑ አገራቸው ከህገ-ወጦች የነጠቀችውን የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ለቻይና በመሸጥ የዱር እንስሳት ጥበቃውን መደጎም ትችላለች የሚል እምነት አላቸው። ፓትሪክ ኦሞንዲ ግን በዚህ አይስማሙም።
«ይህ ችግሩን ለመፍታት መፍትሔ አይሆንም። በ1997 ዓ.ም እና በ2007 ዓ.ም. የማቃጠሉ ድርጊት በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲቀር ተደርጎ ነበር። አሁን የተባባሰው ህገ-ወጥ ዝውውር እና አደን ከሁለቱ ሙከራዎች እናገናኘዋለን። ለዚያም ነው ከደቡብ አፍሪቃ ባልደረቦቻችን ጋር በመሆን በመቀመጥ እንዲህ አይነት ሙከራዎች በቃ ያልንው። በዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ዓለም አቀፍ ንግድ ሙሉ በሙሉ ክልክል ነው።»
የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ እንዲህ በቀላሉ በእሳት የማይያያዝ በመሆኑ ኬንያውያኑ የተለየ ነዳጅ መጠቀም ይኖርባቸዋል። 'እጆቻችሁን ከዝሆኖቻችን ላይ አንሱ' የተሰኘውን ዘመቻ የሚመሩት የዱር እንስሳት ተንከባካቢዋ ዶ/ር ፓውላ ካኹምቡ በመቃጠሉ ይስማማሉ።
«ሌላ ምንም ምርጫ የለም። ለህጋዊው ገበያ ቢሸጥ እንኳ ዞሮ ዞሮ የህገ-ወጥ አደንን ያባብሳል። የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ማስቀመጥ ተመልሶ ሊዘረፍ ይችላል። ለዚያም ነው ሁሉም አገሮች እንዲያቃጥሉ የምናበረታታው። በዚህም ፈጽሞ ተመልሶ ወደ ገበያው ሊገባ አይችልም። መንግስት በዚህ ድርጊት ለህገ-ወጥ አዳኞች ምንም ይቅርታ እንደማያደርግ መልዕክት ያስተላልፋል። ህገ-ወጥ አዳኞችን እና አዘዋዋሪዎችን ፈጽሞ አንታገስም። ከዚህ የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ምንም አይነት ነገር አንሻም። ለእኛ ዝሆኖች በህይወት እያሉ የበለጠ ዋጋ አላቸው።»
የማቃጠል ስርዓቱ አዘጋጆች ነገ ቅዳሜ ከ105 ቶን በላይ የዝሆን ጥርስ እና የአውራሪስ ቀንድ ተቃጥሎ ወደ ጭስነት ሲቀየር መጥታችሁ ታዘቡ ሲሉ ጥሪ አስተላልፈዋል።

Elfenbeinverbrennung in Kenia
ምስል DW/A. Wasike
Afrikanischer Elefant
ምስል CC BY 2.0/Benh LIEU SONG

አንድሪው ዋሲኬ / እሸቴ በቀለ

ሒሩት መለሰ