የኬንያ ድጋሚ ምርጫ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 15 2010ማስታወቂያ
የኬንያ ድጋሚ ምርጫ በታቀደው መሠረት ነገ እንደሚካሄድ የኬንያ የምርጫ ኮሚሽን ዛሬ አስታውቋል። እስከዛሬዋ እለት ድረስ ምርጫው መካሄዱ አጠራጣሪ ነበር። ድጋሚው ምርጫ ለሌላ ጊዜ እንዲገፋ ለቀረበለት ማመልከቻ ዛሬ ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቅ የነበረው የሐገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ሳያዳምጥ ቀርቷል። ፍርድ ቤቱ በዛሬው ችሎት መገኘት ከነበረባቸው ሰባት ዳኞች ሁለቱ ብቻ በመቅረባቸው ኮረም ባለሟሟላቱ ጉዳዩን መስማት እንዳልተቻለ የፍርድ ቤቱ ዋና ዳኛ ዴቪድ ማራጋ ተናግረዋል። በሌላ በኩል ፣ ምርጫው በተጠራበት በነገው እለት ናሳ በሚል ምህጻር የሚጠራው የተቃዋሚዎች ህብረት ናይሮቢ ውስጥ የተቃውሞ ሰልፍ እንዲያካሄድ እንደማይፈቅድ የኬንያ ፖሊስ አስታውቋል። ከድጋሚው ምርጫ ራሳቸውን ያገለሉት የተቃዋሚዎቹ እጩ ራይላ ኦዲንጋ ደጋፊዎቻቸው በነገው ምርጫ ድምፅ ለመስጠት እንዳይወጡ ጥሪ አስተላልፈዋል። ከናይሮቢ ሀብታሙ ስዩም ዘገባ ልኮልናል።
ሀብታሙ ስዩም
ኂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ