1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኬንያ ፣ መያዶች ላይ የወሰደችው ጥብቅ ርምጃ

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 10 2007

የኬንያ መንግሥት ፤ ሽብር ፈጠራን በገንዘብ ይደጋፋሉ ያላቸውን 15 ቡድኖች ጨምሮ ባጠቃላይ በብዙ መቶ የሚቆጠሩ የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች በሕግ የተመዘገቡትን ደንብ ሽሯል።

https://p.dw.com/p/1E7nZ
Kenia President Kenyatta Rede Terroranschläge 02.12.2014
ምስል AFP/Getty Images/S. Maina

ታዛቢዎችደግሞ በደሕንነት ጥበቃ ስም ፣ መንግሥት ሒስ አቅራቢዎችን ሁሉ ፀጥ ለማሰኘት ነው የተነሣሣውበማለት በመንቀፍ ላይ ናቸው። የኬንያ ፣የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች አስተባባሪ ቦርድ ፤ በስም ሳይጠቅስ ፤«አንዳንድ ቡድኖች ለወንጀል ተግባር መሣሪያዎች ሆነው ተገኝተዋል፣ የሽብር ተግባርንም በገንዘብ ይደግፋሉ» በማለት መወንጀሉ ታውቋል። በምሥራቅ አፍሪቃ ፤ ከሞላ ጎደል የተደላደለ ኤኮኖሚና በትጋት የሚሠራ የፕረስ ነጻነት ያላት ሀገር ኬንያ ፣ ለዚህ ርምጃ ምን ይሆን ያነሣሣት? ይህ ዓይነቱ አካሄድ የመድበለ ፓርቲውን ዴሞክራሲያዊ አሠራር ፤ የሰብአዊ መብትንም አያያዝ እስከምን ድረስ ይጎንጥ ይሆን? ዋና ጽ/ቤቱ በፕሪቶሪያ የሚገኘውን ፤ በአፍሪቃ የስልታዊ ጉዳዮች ጥናት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ ጃኪ ሲልዬ ፣ ሰፊና ሥር ነቀል ስለመሰለው ርምጃ እንዲህ ብለዋል።

Nairobi Kenia Abgeordnete Parlament Debatte Sicherheitsgesetz 18.12.2014
ምስል Simon Maina/AFP/Getty Images

«ከ 500 በላይ የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች(NGO) ከምዝገባ ተሽረዋል። አንዳንዶችም፣ የሂሳብ ሰነዳቸው እንዳይንቀሳቀስ ተደርጓል። ይህን የመሰለ ርምጃ ነው የተወሰደው። ክሱ፣ በኬንያና በአፍሪቃ ቀንድ ለወንጀል ተግባር መሣሪያዎች ሆነዋል ፤ በሆቴሎች መስተንግዶ አሸባሪዎችን በገንዘብ በመደገፍ ፣ ድርጅቶቹ ተባብረዋል የሚል ነው። በዚህ ውንጀላ፣የተጠቃለሉት ድርጅቶች በርከት ያሉ ሳይሆኑ አልቀሩም። ይህም በፓርላማ የሚገኙ የሴቶች ቡድኖችን የገጠር የልማት ድርጅቶችንና የመሳሰሉትን ሁሉ ነው የሚያጠቃልለው።»

ከጥቂት ሳምንታት በፊት ኬንያ ውስጥ የድርጅቶችን ተግባር የሚገድብ ደንብ ለፓርላማ ቀርቦ ነበር። ይሁን እንጂ ጉዳዩ ከዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች ጉዳይ መርማሪ ፍርድ ቤት (ICC) አንጻር የተያዘ ዘመቻ ነበረ ማለት ይቻላል። ከ 500 በላይ ከሆኑት የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች ምን ያህሉ በቀጥታ ከሽብር ተግባር ጋር ግንኙነት አላቸው ተብለው እንደተጠረጠሩ ወይም በገንዘብ ረገድ እስከምን ድረስ እንደሚደግፉ ምንም የሚታወቅ ነገር የለም። የኬንያ መንግሥት በሽብር ተግባር ከሚጠረጥራቸው ጥቂት ቡድኖች ባሻገር በሰፊው የመንግሥት ባልሆኑ ድርጅቶች ላይ የሆነ ዓይነት ብቀላ ለማካሄድ አመቺ አጋጣሚ ያገኘ ይመስላል የሚሉ ሐያስያን አልታጡም። ግን ይህን ለማድረግ ምን የተለየ ጉዳይ ወይም ምክንያት አለው? ጃኪ ሲልዬ በይበልጥ ሲያብራሩ---

Nairobi Kenia Abgeordnete Parlament Debatte Sicherheitsgesetz 18.12.2014
ምስል Reuters/T. Mukoya

«የዑሑሩ ኬንያታ መንግሥት፣ የ መንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች ተግባር አሳሳቢ ሆኖበት ቆይቷል። ለዚህ የሚሰጠው ከፊል ምክንያት ስለ ሰብአዊ መብት የሚያቀርቡት ዘገባ መንግሥትን ሲያሳጣውና ሲያሳፍረውም መቆየቱ ይታወቃልና! በተወሰነ ደረጃ አንዳንዶቹ መፍቀሬ ICC ወገኖች ኬንያ ውስጥ ዘመቻ ያካሄዱበት ሁኔታ አልተረሳም። እርግeጥ አገሪቱ ጠንካራ የሲብል ማሕበረሰብ ያላት ናት። በሺ ባይሆን እንk/ በመቶዎች የሚቆጠሩ ለማሕበረሰቡ ሰፊ አገልግሎት የሚሰጡ የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች አሉ። የኬንያ መንግሥት ይህን ርምጃ ለመውሰድ ምን እንደገፋፋው ከሩቅ ሆኖ ጠንቅቆ ለማወቅ ያስቸግራል። ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ለአልሸባብ ተደርጓል መባሉ ብቻ ሳይሆን፣ እንደ እኔ ጥርጣሬ የኬንያ መንግሥት ICC በፕሬዚዳንት ኬንያታ ላይ ይዞት የነበረውን የክስ ጉዳይ እንዲያጠናክር አለቅጥ ግፊት ያደርጉ በነበሩ ድርጅቶች ላይ ለመበቀል ያህል ርምጃ ወስዷል ነው የምለው። »

የአፍሪቃ ቀንድ ፤ ከድጡ ወሰማጡ በመረማመድ ያለ አካባቢ ነው የሚመስለው፣ በተለይ ሰብአዊ መብት ፤ የፕረስ ነጻነት ፣ በአጠቃላይም የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሲነሣ! ይህ ያሁኑ ኬንያ የተከተለችው የሂደት አቅጣጫ ወዴት ነው የሚያመራው?

Kenianisches Parlament debattiert über neues Sicherheitsgesetz - Polizei
ምስል AFP/Getty Images/S. Maina

«የአፍሪቃ ቀንድ ፤ ከሁሉም የአፍሪቃ አካባቢዎች በላቀ ሁኔታ መረጋጋት የማይታይበት ነው ምክንያቱም፤ ሱዳን ፤ ደቡብ ሱዳን፤ ሶማልያና ኢትዮጵያን የመሳሰሉ ጭካኔ በተመላበት ውስጣዊ ውዝግብ ያለፉ ሲሆን ወደ ደቡብ ወረድ ብሎም የታላላቆቹ ሃይቆች አካባቢ አለ።ይህ ሁሉ መረጋጋት የማይታይበት የአፍሪቃ ክፍል ነው።

ኬንያ፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ከሶማልያ ለየት ያለ ችግር ተጋርጦባታል። በመጨረሻ ፣ የአፍሪቃን ሕብረት ሰላም አስከባሪ ጦር(አሚሶም)ን ለመርዳት ጣልቃ መግባቷና በአሸባብ አጸፋዊ ርምጃ እንደወሰደባት ዐይተናል። አሁን ፤ አሳሳቢው ጉዳይ ፣ የኬንያ መንግሥት በተጋነነ፣ «አይጥ በበላ---» ዓይነት አጸፋዊ ርምጃ መውሰዱ ይሆን?! የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶችን ስለሚመለከተው እገዳ፣ ዝርዝሩን ጠንቅቀን አናውቀውም። ግልጽ የሆነ ማብራሪያም ሆነ ትክክለኛ ሒስ ለመሰንዘር ፣ አስቸጋሪ ነው። በሂደት ፣ ሁኔታው ምናልባት ይበልጥ ግልጽ ይሆናል!። »

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ